በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት

Public Relation

የዶሮ ልማት ፕሮጀክትን አስመልክቶ የውይይትና የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃግብር ተካሄደ!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 17/2018 ዓ.ም በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በዲላ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የተጀመረው የዶሮ ልማት ፕሮጀክት ውጤታማ እንዲሆን የደብሩ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስተዳደርና የልማት ኮሚቴ አባላት ለሥራው ልዩ ትኩረት እንዲሰጡ የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃግብር ተካሄደ። ይህ የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃግብር የተካሄደው የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅና የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ብርሃኑ ክፍሌ እንዲሁም ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ነው። ​የመርሃግብሩ ዋና ዓላማ የደብሩ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስተዳደርና የልማት ኮሚቴው ለፕሮጀክቱ አስፈላጊውን ዝግጅት እንዲያደርጉና ለሥራው መፋጠን በትጋት እንዲነሳሱ ግንዛቤ መፍጠር ነው። በውይይቱ ወቅት የልማት ኮሚቴውና የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አባላት በፕሮጀክቱ አፈጻጸም፣ በሚጠበቁ ውጤቶችና ሊያጋጥሙ በሚችሉ ተግዳሮቶች ዙሪያ ሰፊ ውይይት ካደረጉ በኋላ የበኩላቸውን ገንቢ ሃሳቦችን አቅርበዋል። የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሕይወት ብርሃኑ ክፍሌ ከብፁዕነታቸው በሚሰጣቸው አባታዊ መመሪያ መሰረት በፕሮጀክቱ ዙርያ ሰፊ ሥራ እንደተሠራ እንዲሁም ከዚህም በኋላ በርካታ ሥራዎችን ለመሥራት ቅድመ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ገልጸዋል። ​ብፁዕነታቸው የቀረቡትን ሃሳቦች መነሻ በማድረግ በሰጡት አባታዊ ግንዛቤ ማስጨበጫ ንግግር፤ ቤተ ክርስቲያን ያሏትን ሀብቶች ተጠቅማ ሙዳየ ምጽዋትን ለዓላማው ማዋልና ራሷን በኢኮኖሚ መቻል እንዳለባት አስገንዝበዋል። የዶሮ ልማት ፕሮጀክቱ የደብሩን ገቢ ከማሳደግ ባለፈ፣ ለሌሎች አድባራትና ገዳማት ተምሳሌት የሚሆን ሥራ መሆኑን ገልጸው፤ የሰበካ ጉባኤውና የልማት ኮሚቴው በኃላፊነት ስሜትና በቁርጠኝነት ሊንቀሳቀሱ እንደሚገባ መመሪያ ሰጥተው በጸሎት ፈጽመዋል።

የዶሮ ልማት ፕሮጀክትን አስመልክቶ የውይይትና የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃግብር ተካሄደ! Read More »

ከ178 ሺህ ብር በላይ የሚያወጡ ንዋየ ቅድሳት ለገጠር አብያተ ክርስቲያናት ድጋፍ ተደረገ!

​ኤክቱስ ታኅሣሥ 16/2018 ዓ.ም ​በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ዲላ ማዕከል የንዋየ ቅድሳት እጥረት ላለባቸው አብያተ ክርስቲያናት ማለትም በይርጋጨፌ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር ለሚገኘው ለኤላ ጠነቻ ቅዱስ ዑራኤል፣ በቡሌና ረጴ ወረዳዎች ቤተ ክህነት ሥር ለሚገኘው ለላባ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና በኮሬ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር ለሚገኘው ለቆሬ ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት የሚውል የንዋየ ቅድሳት ድጋፍ አስረክቧል። ማዕከሉ ከበጎ አድራጊ ምዕመናን ያስተባበረው ይህ ድጋፍ በገንዘብ ሲሰላ በድምሩ 178,230 (አንድ መቶ ሰባ ስምንት ሺህ ሁለት መቶ ሠላሳ) ብር የሚያወጣ መሆኑ ተገልጿል። ​በርክክብ መርሃ ግብሩ ላይ የማኅበረ ቅዱሳን ዲላ ማዕከል የጽሕፈት ቤት ኃላፊ ምንላርግህ የትዋለ እና የማዕከሉ ሙያ፣ ገዳማት እና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች አገልግሎት ክፍል ኃላፊ ለዓለም ድብቁ ተገኝተው ድጋፉን ለሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ለሆኑት ለብፁዕ አቡነ ገሪማ አስረክበዋል። ብፁዕነታቸውም ድጋፉን ከተረከቡ በኋላ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መሳለጥ ይህንን ተግባር ለፈጸሙ ምዕመናን ጸሎትና ቡራኬ ያደረጉ ሲሆን ይህንን መሰል ድጋፎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አባታዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። ​ብፁዕነታቸው ከማዕከሉ ኃላፊዎች የተረከቧቸውን ንዋየ ቅድሳትና አልባሳት በአገልግሎት እጥረት ለሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት እንዲደርስ አስረክበዋል። በዚህም መሠረት ብፁዕነታቸው በይርጋጨፌ ወረዳ ለሚገኘው ኤላ ጠነቻ ቅዱስ ዑራኤል፣ በቡሌና ረጴ ወረዳዎች ለሚገኘው ለላባ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ እንዲሁም በኮሬ ወረዳ ለሚገኙት ለጂጆላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ለኬሬዳ ቅድስት ሥላሴ፣ ለጉልቤ ቅድስት ማርያም እና ለጉሙሬ ኢየሱስ አብያተ ክርስቲያናት ተደራሽ እንዲሆኑ ለየወረዳ ቤተ ክህነቱ ሥራ አስኪያጆችና ጸሐፊዎች ተረክበዋል። ​ይህ በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት የተከናወነው ተግባር ሀገረ ስብከቱ ከዚህ ቀደም የሚተገብረው ተግባር ሲሆን በገጠር አካባቢ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓተ አምልኮንና ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን ያለ ንዋየ ቅድሳት ችግር በተሟላ ሁኔታ እንዲያከናውኑ ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑ ተጠቁሟል።

ከ178 ሺህ ብር በላይ የሚያወጡ ንዋየ ቅድሳት ለገጠር አብያተ ክርስቲያናት ድጋፍ ተደረገ! Read More »

በዲላ ከተማ ለሚገነባው የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ የገቢ ማስገኛ ሎተሪ መዘጋጀቱ ተገለጸ!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 16/2018 ዓ.ም ​በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በዲላ ከተማ ለሚያስገነባው የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ ለገቢ ማስገኛ የሚሆን የሎተሪ ዕጣ መዘጋጀቱን ሀገረ ስብከቱ አስታውቋል። ይህ ታላቅ መንፈሳዊ ፕሮጀክት ከብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ መቀመጫነት ባለፈ በሀገረ ስብከቱ የሚከናውኑ ልዩ ልዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶች የሚከናወኑበት መሆኑ ተገልጿል። ​በዛሬው ዕለት በተከናወነው የሎተሪ ማከፋፈያ መርሃ ግብር ላይ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ገሪማ የተገኙ ሲሆን ሥራው በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ የሁሉም ሰው ኃላፊነት መሆኑን አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል። ብፁዕነታቸው እንዲህ ያሉ የልማት ሥራዎች የቤተ ክርስቲያንን ክብር ከማስጠበቅ ባለፈ ምእመናን በረከት እንዲያገኙ ዕድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። ​በመርሃ ግብሩ ላይ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሕይወት ብርሃኑ ክፍሌ፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ፣ የየክፍል ኃላፊዎች፣ የየወረዳ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጆችና ጸሐፍት፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎች እና የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ አሠሪ ኮሚቴዎች ተገኝተዋል። ​ሀገረ ስብከቱ ለገቢ ማስገኛው ያዘጋጀውን ይህንን የሎተሪ ዕጣ ለስድስቱ ወረዳ ቤተ ክህነትና ለማኅበረ ቅዱሳን ዲላ ማዕከል በዛሬው ዕለት አከፋፍሏል። ​ይህ በዲላ ከተማ የሚገነባው የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ ግንባታው ሲጠናቀቅ የሀገረ ስብከቱ ለመንፈሳዊ አገልግሎት መሳለጥ ከፍተኛ ፋይዳ እንደሚኖረው ታምኖበታል። ዕጣው የሚወጣበትን ቀን ሀገረ ስብከቱ የሚያሳውቅ ይሆናል።

በዲላ ከተማ ለሚገነባው የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ የገቢ ማስገኛ ሎተሪ መዘጋጀቱ ተገለጸ! Read More »

ታኅሣሥ 19 ለሚከበረው የቅዱስ ገብርኤል በዓል እየተደረገ ያለው የቅድመ ዝግጅት ሥራ በብፁዕ አቡነ ገሪማ ተጎበኘ!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 14/2018 ዓ.ም ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል በጪጩ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ለሚከበረው ዓመታዊ የታኅሣሥ 19 የቅዱስ ገብርኤል የንግሥ በዓል እየተደረጉ ያሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን በቦታው ተገኝተው ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ፣ የሀገረ ስብከቱ የፕሮጀክት ማናጀር ቀሲስ ጤናው እንዳላማው፣ የጪጩ ቀበሌ የኢንዱስትሪ ቀጠና አስተዳደር አቶ ብርሃኑ፣ የወረዳ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጠበብት መሪጌታ መሰረት፣ የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ኃይል ሀብቴ ገብረ ሕይወት እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። ብፁዕነታቸው በጉብኝታቸው በደብሩ እየተከናወኑ ያሉ የጽዳት ሥራዎችን የተመለከቱ ሲሆን በተለይም ደብሩ ራሱን በራሱ ለመቻል እያከናወናቸው ያሉ የልማት ሥራዎችን ተመልክተዋል። በደብሩ ቅጥር ግቢ ውስጥ የለሙትና የአካባቢው መገለጫ የሆኑት የቡና እና የእንሰት ተከላ ሥራዎች፣ እንዲሁም ለአካባቢው ማህበረሰብ አገልግሎት ለመስጠት ቅድመ ዝግጅቱን ያጠናቀቀውን የወፍጮ ቤት እንቅስቃሴ በብፁዕነታቸው ተጎብኝቷል። በሌላ በኩል የደብሩ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለበዓሉ የሚመጡ ምዕመናን የሚጠቀሙባቸውን የጧፍ ምርቶች በስፋት በማዘጋጀት ላይ የሚገኙ ሲሆን ይህም የወጣቶች በቤተክርስቲያን አገልግሎትና ልማት ላይ ያላቸውን ተነሳሽነት የሚያሳይ መሆኑ ተገልጿል። የደብሩ አስተዳዳሪ በበኩላቸው በደብሩ ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ የግብርና እና የተለያዩ ዘርፈ ብዙ ልማቶች ያሉበትን ደረጃ ለብፁዕነታቸው አስረድተዋል። በጉብኝቱ ወቅት የተገኙት የጪጩ ቀበሌ የኢንዱስትሪ ቀጠና አስተዳደር አቶ ብርሃኑ በበኩላቸው በዓሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ብቻ ሳይሆን የአካባቢው ማኅበረሰብ ሁሉ በጉጉት የሚጠብቀው ታላቅ በዓል መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በዓሉ በሰላም እንዲጠናቀቅ ከአካባቢው ማህበረሰብ ጋር በመተባበር ከጸጥታና ከጽዳት አንጻር በርካታ ሥራዎች በኅብረት እየተከናወኑ መሆኑን ለብፁዕነታቸው አስረድተዋል። ብፁዕ አቡነ ገሪማ በጉብኝታቸው ማጠቃለያ ላይ ባስተላለፉት መልእክት ደብሩ ከመንፈሳዊ አገልግሎት በተጨማሪ በልማትና በአካባቢ ጥበቃ ረገድ እያከናወነ ያለው ተግባር የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ከአካባቢው አስተዳደርና ከነዋሪው ማኅበረሰብ ጋር ያለው ጠንካራ ትብብር ለበዓሉ ስኬታማነትና ለደብርይ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን በመጥቀስ ለዝግጅቱ ስኬት ለደከሙ አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበው በጸሎት ፈጽመዋል።

ታኅሣሥ 19 ለሚከበረው የቅዱስ ገብርኤል በዓል እየተደረገ ያለው የቅድመ ዝግጅት ሥራ በብፁዕ አቡነ ገሪማ ተጎበኘ! Read More »

በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት መንፈሳዊ አገልግሎትን ከልማት ጋር የሚያቀናጅ የዶሮ እርባታ ፕሮጀክት በይፋ ተጀመረ!!!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 11/2018 ዓ.ም በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በዲላ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል እና በአንዲዳ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም አብያተ ክርስቲያናት ገቢን ለማጠናከርና የአብነት ተማሪዎችን በቋሚነት ለመርዳት የታለመ የዶሮ እርባታ ፕሮጀክት በይፋ ተጀምሯል። ይህ ተስፋ ሰጪ የልማት ሥራ በዶ/ር ሙሉእመቤት ወርቁ አነሳሽነት እንዲሁም በላዕከ ወንጌል ያሬድ አደመ እና በወ/ሪት ሰላም አያሌው አስተባባሪነት የተጀመረ ነው። በመጀመሪያው ዙር በዲላ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን 250 የሥጋ ዶሮዎች እንዲሁም በአንዲዳ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን 100 የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች እንዲገቡ ተደርጓል። ለሥራው ስኬታማነትም የዓለም አቀፍ የእንስሳት ምርምር ተቋም (ILRI) ሰራተኛና ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ወንድሜነህ እሳቱ፣ ዶ/ር አሉላ አለማየሁ እና ዶ/ር መኮንን ግርማ ዶሮዎችን ከአዲስ አበባ በማምጣት፣ በማስገባትና የማስጀመር ሥራውን በማከናወን ሙያዊ ፣ የቁስ እና የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል። ከዲላ መንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት ከሚገኙ 13 አብያተ ክርስቲያናት ለተውጣጡ 24 ሰልጣኞች በዘርፉ ባለሙያዎች ስለ ዶሮ እርባታ ጥልቅ ስልጠና ተሰጥቷል። ስልጠናውም፦•  ጥምር ጠቀሜታ ያላቸው ዶሮዎች እርባታ፤•  የዶሮ መኖ አዘገጃጀት፤•  ሳይንሳዊ የዶሮ እንክብካቤና ጤና አጠባበቅ እና•  የዶሮ እርባታ ትርፋማነት ላይ ያተኮረ ነበር። ሰልጣኞቹ በሰጡት አስተያየትም “ይህ ስልጠና ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን ሰፊ መሬትና የሰው ኃይል በመጠቀም እንዴት ውጤታማ መሆን እንደምትችል ዓይን ከፋች ሆኖልናል፤ ወደ ተግባር ለመግባትም ተዘጋጅተናል” ብለዋል። የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገሪማ በዕለቱ ተገኝተው  ይህ ፕሮጀክት እውን እንዲሆን ያስተባበሩትን፣ ድጋፍ ያደረጉትንና ስልጠና የሰጡ ባለሙያዎችን አመስግነው ሀገረ ስብከቱ የፕሮጀክቱ ባለቤት በመሆን ወደ ትግበራ እንደተገባና ወደፊትም አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ እንደሚያደርግ በመግለጽ አባታዊ የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል። ብፁዕነታቸው በመልእክታቸውም “ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎቷን በስፋት ለማከናወን ራሷን በኢኮኖሚ መደገፍ ይኖርባታል። ይህ የዶሮ እርባታ ፕሮጀክት የአካባቢውን ምዕመናንና ማህበረሰብ ተጠቃሚ ማድረግ የሚችልና የአብነት ተማሪዎቻችንን ለመመገብና የቤተ ክርስቲያንን ገቢ ለማሳደግ ትልቅ ፋይዳ አለው” በማለት አሳስበዋል። በዕለቱ እንግዶች በአንዲዳ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ የአብነት ተማሪዎችን በመጎብኘት የትምህርት ሂደታቸውን ተመልክተዋል።

በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት መንፈሳዊ አገልግሎትን ከልማት ጋር የሚያቀናጅ የዶሮ እርባታ ፕሮጀክት በይፋ ተጀመረ!!! Read More »

ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤና በዓለ ንግሥ በጪጩ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከታኅሣሥ 17-19 2018 ዓ.ም ስለተዘጋጀ ሁላችሁም እንድትሳተፉ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 10/2018 ዓ.ም

ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤና በዓለ ንግሥ በጪጩ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከታኅሣሥ 17-19 2018 ዓ.ም ስለተዘጋጀ ሁላችሁም እንድትሳተፉ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን! Read More »

ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሒሳብ አያያዝን ለማዘመን የሚያስችል ውይይት ከአስተዳደር አካላት ጋር አደረጉ!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 7/2018 ዓ.ም ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የሀገረ ስብከቱን የፋይናንስ አስተዳደር ለማሻሻል የሚያስችል ውይይት ከአስተዳደር አካላት ጋር አደርገዋል። የውይይቱ ዋና ትኩረት የሀገረ ስብከቱ ጽሕፈት ቤት ሲጠቀምበት የቆየውን ድርብ የሒሳብ አመዘጋገብ (Double-Entry Accounting) ሥርዓት በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ተግባራዊ ማድረግ ላይ ነበር። የሀገረ ስብከቱ የፕሮጀክት ማናጀር ቀሲስ ጤናው እንዳላማው ስለ ድርብ የሒሳብ አመዘጋገብ (Double-Entry) አስፈላጊነት ሰፋ ያለ ገለጻ አድርገዋል። ይህ ሥርዓት እያንዳንዱ ገንዘብ በሁለት የሒሳብ መዝገቦች መመዝገብ እንዳለበት የገለጹ ሲሆን ይህም የሒሳብ ስህተቶችን ለመቀነስ እና የገንዘብ አያያዝን ሚዛናዊ (Balanced) ለማድረግ እንደሚረዳ ተናግረዋል። በውይይቱ የተሳተፉት የአድባራት አስተዳዳሪዎችና የአስተዳደር አካላት ሀገረ ስብከቱ ይህንን ዘመናዊ ሥርዓት ወደ አድባራት ለማውረድ እየሠራ ያለው ሥራ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ገንዘብ በአግባቡ እና በግልጽነት ማስተዳደር እንዲቻል ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው የገለጹ ሲሆን ሥራውን ሙሉ ለሙሉ ተፈጻሚ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። ይህንን የዘመናዊ የሒሳብ ሥራ በብቃት ለመምራት የሚያስችል የሰው ኃይልን ለማጠናከር በአካውንቲንግ የትምህርት ዘርፍ የተመረቀ እና የሒሳብ ሥራዎችን በብቃት ለመሥራት የፒችትሪ (Peachtree) አመዘጋገብ ሶፍትዌር ዕውቀት ያለው ሰው እንዲቀጠር ተወስኗል። ይህ ቅጥር ሀገረ ስብከቱ በፋይናንስ አያያዝ ሂደት ግልጽነትን እና የሥራ ቅልጥፍናን ለማምጣት ያለውን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተገልጿል። በውይይቱ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ፣ የሀገረ ስብከት የክፍል ኃላፊዎች፣ የመንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና ጸሐፊ፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎችና የአስተዳደር አካላት ተገኝተዋል።

ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሒሳብ አያያዝን ለማዘመን የሚያስችል ውይይት ከአስተዳደር አካላት ጋር አደረጉ! Read More »

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ለመካነ ቅድስት ሥላሴ ወአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ለዋለሜ ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት እና ለገደብ ደብረ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናት ለመጽሐፍ መምህራን የተዘጋጀ የፈተና ውጤት!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 6/2018 ዓ.ም

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ለመካነ ቅድስት ሥላሴ ወአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ለዋለሜ ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት እና ለገደብ ደብረ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናት ለመጽሐፍ መምህራን የተዘጋጀ የፈተና ውጤት! Read More »

አንድ መቶ ሠላሳ ሁለት አዳዲስ አማንያን በብፁዕ አቡነ ገሪማ ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አገኙ!!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 5/2018 ዓ.ም በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በመንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት በቆቲ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቅድመ ጥምቀት መደበኛ ትምህርት ከተማሩ አንድ መቶ አርባ ዘጠኝ ንዑሰ ክርስቲያን መካከል ሰባ ስምንት ወንድ እና ስድሳ ሦስት ሴት በድምሩ አንድ መቶ ሠላሳ ሁለቱ በዛሬው ዕለት በብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አግኝተዋል። ኢ-አማንያን ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዲመለሱና የሥላሴን ልጅነት እንዲያገኙ ማድረግ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቀዳሚ ተልእኮ ከመሆኑ አንጻር ሀገረ ስብከቱ ይህንን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት እያስፈጸመ ይገኛል። አዳዲስ አማንያንን የማስጠመቁን ሥራ የደብሩ ስብከተ ወንጌል ከደብሩና ከወረዳ ቤተ ክህነቱ ጋር በመናበብ የተሠራ ሲሆን በቀጣይ ደግሞ አስራ ሰባት አዳዲስ አማንያንን ለማስጠመቅ ቅድመ ዝግጅታቸውን መጨረሳቸውን ገልጸዋል። በዕለቱ የዕለቱን ትምህርት የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ በጌዴኡፋ ቋንቋ አስተምረዋል። በመጨረሻም ብፁዕነታቸው በጌዴኡፋ እና በአፋን ኦሮሞ ዝማሬ ዘምረው እንዲሁም አዳዲስ የተጠመቁ ምዕመናንን ማጽናት እንደሚገባ ገልጸው በአፋን ኦሮሞ እና በአማርኛ ቋንቋዎች ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጥተው በጸሎት ፈጽመዋል። በመርሃግብሩ ላይ የሀገረ ስብከቱ የመንፈሳዊ ትምህርትና የካህናት አገልግሎት ክፍል ኃላፊ መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ዮሐንስ ምሕረቱ፣ የወረዳ ቤተ ክህነቱ ዋና ጸሐፊ ሊቀ ኅሩያን እሸቱ ማሞ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ምዕመናን ተገኝተዋል።

አንድ መቶ ሠላሳ ሁለት አዳዲስ አማንያን በብፁዕ አቡነ ገሪማ ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አገኙ!! Read More »

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት የአንዲዳ የአዳሪ አብነት ትምህርት ቤት አምስት የትርጓሜ ተማሪዎችን ተቀብሎ በአዳሪነት ማስተማር ይፈልጋል።

ኤክቱስ ታኅሣሥ 2/2018 ዓ.ም

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት የአንዲዳ የአዳሪ አብነት ትምህርት ቤት አምስት የትርጓሜ ተማሪዎችን ተቀብሎ በአዳሪነት ማስተማር ይፈልጋል። Read More »

Scroll to Top