“ምእመናን በሃይማኖት እንዲጸኑ ሰላምን፣ፍቅርን እና አንድነትን ስበኩ!” ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ
በዛሬው ዕለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም የበላይ ኃላፊ፣ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣የደቡብ ምሥራቅ ትግራይና የራያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ሕዝቄል የከፋና ሸካ፣ቤንች ሸኮ እና ምዕራብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስና የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኀላፊ እና ሌሎች ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እግዶች በተገኙበት የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በትርጓሜ መጻሕፍትና በነገረ መለኮት የትምህርት ዘርፍ በቀን እና በማታ ያስተማራቸውን 769 ደቀ መዛሙርትን አስመርቋል። ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት መልእክት ምእመናን ትእዛዘ እግዚአብሔርን እንዲጠብቁ፣በምግባር እንዲጎለብቱና በሃይማኖት እንዲጸኑ ሰላምን፣ፍቅርን እና አንድነትን በመስበክ የማስተማር ኃላፊነታችሁን ተወጡ ሲሉ ተመራቂዎችን አሳስበዋል፡፡ አክለውም ጌታችን ሐዋርያትን ሂዱና አስተምሩ ብሎ እንደላካቸው ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን መሠረት አድርጋ በየዓመቱ ተማሪዎችን እያስመረቀች ትገኛለች ያሉ ሲሆን ሰላም ከሌለ ምንም አይኖርም ስለዚህም መቻቻል እንዲኖር፣አንድነት እንዲሰፍን እንዲሁም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግብ እንዲሳካ ድርሻችሁን መወጣት ይጠበቅባችኋል ብለዋል፡፡ የኮሌጁ የበላይ ኀላፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቄል በበኩላቸው ነፍስን እና ሥጋን የሚጠግን፣የሚያለመልምና የሕይወት ውኃ ትምህርት በመሆኑ ደቀ መዛሙርቱ በተማሩት ትምህርት መሠረት በሚሄዱበት ሁሉ የዓለሙን ፈተና ተቋቁመው ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል እንዳለባቸው ተናግረዋል። በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ በተመራቂዎች ወረብና ቅኔ የቀረበ ሲሆን ከፍተኛ ውጤት ያመጡ ተማሪዎች ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ የሰዋስወ ብርሃን ቅዱ ስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት በሚል ስያሜ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትንና መምህራንን ማሠልጠኛ እንዲሆን በ1930 ዓ.ም ተመሥርቶ በአሁኑ ወቅት ከ82 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡
“ምእመናን በሃይማኖት እንዲጸኑ ሰላምን፣ፍቅርን እና አንድነትን ስበኩ!” ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ Read More »








