በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት

Admin

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት ሥር የሚገኙ ሦስት ዞኖችን በማካተት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ የሚያከናውን መዋቅር ነው። ሀገረ ስብከቱ ከመዲናዋ አዲስ አበባ በ365 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው የዲላ ከተማ የመንበረ ጵጵስና መቀመጫውን (ማዕከልነቱን) አድርጎ የሚንቀሳቀስ የቤተ ክህነት አስተዳደር ነው። ​ምንም እንኳን ሀገረ ስብከቱ በአሁኑ የሀገረ ስብከት አደረጃጀቱ ጥቅምት 21 ቀን 2012 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ቢቋቋምም በአካባቢው ያለው የኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ግን የቆየ መሠረት አለው። ከእነዚህም መካከል በኮሬ ዞን የሚገኘው የየሮ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መመሥረቱ በአካባቢው የነበረውን ጥንታዊ የሃይማኖት እንቅስቃሴ የሚያሳይ ዋነኛ ማስረጃ ነው። ​በተመሳሳይ በ፲፱ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በ1882 የተመሰረተው የቡሌ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ፣ በ1891 የተመሰረተው የመንዶ ቅዱስ ሚካኤል፣ በ1895 የተመሰረተው የላባ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በ1827 የተመሰረተው የጪጩ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በ1892 የተመሰረተው የገርቦታ ደብረ ፀሐይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በ1891 የተመሰረተው የሲጊጋ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንደአብነት በአካባቢው ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ማኅበረሰብ ዘንድ ለረጅም ዘመናት የቆየ መንፈሳዊ ተደራሽነት እንደነበራት ማሳያ ነው። ይህ ታሪካዊ መሠረት ሀገረ ስብከቱ አሁን ላለው መዋቅራዊ እድገት እንደ መነሻ ሆኖ ሊያገለግል ይችላል። ​የሀገረ ስብከቱ ራሱን ችሎ መቋቋም አስፈላጊ የሆነው ቀድሞ የነበረው የሲዳማና ጌዴኦ ዞኖች አማሮና ቡርጂ ልዩ ወረዳዎች ሀገረ ስብከት መዋቅር እጅግ ሰፊ በመሆኑ እና ለመንፈሳዊ አገልግሎት ተደራሽ አለመሆኑ ነው። ይህ ሰፊ መልክዓ ምድር ለአስተዳደር ምቹ ባለመሆኑ በአብያተ ክርስቲያናት ላይ የሚደረገው የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ተዳክሞ ቆይቷል። ​በዚህ ምክንያት በአካባቢው ያለው የምዕመናን ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ መምጣቱ ለሀገረ ስብከቱ መመሥረት ዋነኛው ምክንያት ሆኗል። አገልግሎቱን ወደ ምዕመኑ ለማቅረብና የአቅም ችግር ላለባቸው አብያተ ክርስቲያናት መልሶ ለማጠናከር ስፋቱን ማጥበብና ራሱን የቻለ አመራር መስጠት የግድ ነበር። ​ሀገረ ስብከቱ ከተመሰረተ በኋላ ባሉት የመጀመሪያዎቹ ዓመታት በሲዳማ ሀገረ ስብከት ብፁዕ ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ ይመራ ነበር። በዚህም አሰራር በርካታ ሥራዎች የተሠሩ ቢሆኑም ይህ ሁኔታ ሀገረ ስብከቱ ራሱን በቻለ አቅም እንዲንቀሳቀስና አስፈላጊ የሆኑ አገልግሎቶችን እንዲያከናውን ዕድል ሳይሰጠው ለጥቂት ዓመታት ቆይቷል። ​ይህንን ክፍተት ለመሙላት በ2015 ዓ.ም ቅዱስ ሲኖዶስ ብፁዕ አቡነ ገሪማን ሀገረ ስብከቱን በቋሚነት እንዲመሩ ሾመ። ​በአሁኑ ወቅት ሀገረ ስብከቱ አገልግሎቱን በስድስት የወረዳ ቤተ ክህነት መዋቅሮች በኩል ያከናውናል። እነዚህም የዲላ እና ወናጎ(በተለምዶ መንበረ ጵጵስና)፣ የይርጋጨፌ፣የኮቾሬ ገደብና ጮርሶ፣ የቡሌና ረጴ፣ የኮሬ ዞን እንዲሁም የቡርጂ ዞን ወረዳ ቤተ ክህነቶች ናቸው። ​በእነዚህ ስድስት ወረዳዎች ስር በአጠቃላይ 78 አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ። ይኸውም በዲላና ወናጎ 17፣ በይርጋጨፌ 15፣ በቡርጂ 15፣ በኮቾሬ ገደብና ጮርሶ 13፣ በኮሬ 11 እና በቡሌና ረጴ 7 አብያተ ክርስቲያናት ናቸው።​ምንም እንኳን መዋቅራዊ አደረጃጀቱ አሁን ከበፊቱ የተሻለ ደረጃ ላይ ቢደርስም ሀገረ ስብከቱ የሚጠበቀውን ያህል ውጤት እንዳያመጣ እንቅፋት የሆኑ በዋናነት አራት ተጨባጭ ችግሮችን መጥቀስ ይቻላል። ​በሀገረ ስብከቱ ውስጥ የሚታየው የሰባኪያነ ወንጌል እጥረት፣ ምዕመናን ስለ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በቂ ግንዛቤ እንዳይኖራቸው አድርጓል። ይህን ክፍተት ለመሙላት ሀገረ ስብከቱ ለባለ ድርሻ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ግንዛቤ በመፍጠር ችግሮችን ለመፍታት እየሠራ ይገኛል። ሆኖም ይህ በቂ ባለመሆሙ ምክንያት የምዕመናንን ቁጥር በተፈለገው መጠን ልክ ማብዛት አልተቻለም። ​ 2. የአብነት ትምህርት ቤት አለመኖር በሀገረ ስብከቱ ውስጥ አንድም የአብነት ትምህርት ቤት አለመኖሩ ሌላኛው ችግር ነው። አብነት ትምህርት ቤት አገልጋዮችን ለማፍራት መሠረት ቢሆንም በሀገረ ስብከቱ ውስጥ ባለመኖሩ ምክንያት አዳዲስ ተተኪ አገልጋዮችን የማግኘት ዕድል እጅግ አነስተኛ ነው።ከዚህ ቀደም በነበረው ሁኔታ የተወሰኑ አገልጋዮችን ማፍራት የተቻለው በከተማ የሚገኙ ጥቂት አብያተ ክርስቲያናት በጎ ፈቃድ ያላቸውን ካህናት በመመደብ ልጆችን በመሰብሰብ በሚሰጡት መሠረታዊ መንፈሳዊ ትምህርት ብቻ ነው። ይህ ሁኔታ ለሀገረ ስብከቱ የወደፊት የአገልጋይ ፍላጎት አስተማማኝ መፍትሔ አይደለም። ለዚህም መፍትሄ እንዲሆን ሀገረ ስብከቱ በአንዲዳ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ የመቃብር ቤቶችን በማደስ፣ ማደሪያ በማዘጋጀት፣ መምህር በመቅጠር እና አስፈላጊውን ሁሉ ግብዓት በጎ አድራጊ ምዕመናንን በማስተባበር የተወሰኑ ደቀ መዛሙርትን እያስተማረ ይገኛል። በተጨማሪም ከደብሩ መሬት በመውሰድ እና በመግዛት አዲስ የአብነት ትምህርት ቤት በማኅበረ ቅዱሳን እየተገነባ ይገኛል። ቢሆንም የመማር ማስተማር ሂደቱ በጎ ፈቃደኛ ምዕመናንን በማስተባበር እንጂ ቋሚ ገቢ የለውም። በአገልጋይ እጥረትና በንዋየ ቅድሳት እጥረት ምክንያት በርካታ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ተዘግተው መቆየታቸው ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ ነው። እነዚህ አጥቢያዎች አገልግሎት አለመስጠታቸው በአካባቢው የሚገኘው ምዕመን ከመንፈሳዊ ሕይወት እንዲርቅና ወደ ሌላ ምርጫ እንዲያመራ አድርጎታል።​ሀገረ ስብከቱ እነዚህን የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት መልሶ ለመክፈትና አስፈላጊውን ግብዓት ለማሟላት ጥረት እያደረገ ቢሆንም፣ ያለው አቅም ግን ከችግሩ ስፋት ጋር ሲነጻጸር ገና ብዙ ሥራ እንደሚቀረው ያሳያል። ይህ በገጠር የሚገኝን ምዕመን የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያገኙ የማድረግ ሥራ የሀገረ ስብከቱ ቀዳሚ ተግባር ነው። ከዚህ ቀደም ሀገረ ስብከቱ የሚከተለው ዘመኑን ያልዋጁ እና ኋላ ቀር አሠራሮችን ነበር። ይህንን​የአስተዳደር ሥርዓቱንም ዘመኑን ወደ ዋጀና ቀልጣፋ ወደ ሆነ አሠራር የመቀየር አስፈላጊነት አሁንም በሀገረ ስብከቱ ዘንድ ይታመናል። ይህንንም ለማሳካት ሀገረ ስብከቱ በሒሳብ ሥራ ረገድ ከዚህ ቀደም የሚከተለው ኋላ ቀር አመዘጋገብ የሆነውን የነጠላ የሒሳብ አመዘጋገብ የሚከተል ሲሆን ይህንን ሥራውን አዘምኖ የድርብ አመዘጋገብ ሂደትን ተግባራዊ አድርጓል። ሀገረ ስብከቱ መረጃዎችን በማሰራጨት ረገድ ዌብሳይት አዘምኖ መረጃ እያሠራጨ ይገኛል። በተጨማሪም በተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያዎች ማለትም በፌስቡክ፣ በቴሌግራም፣ በቲክቶክ፣ በኢንስታግራም ኤክቱስ የተባለ ገጽ በመክፈት መረጃዎችን በንቃት እያሰራጨ ይገኛል። ​እንዲሁም ከዚህ ቀደም ሀገረ ስብከቱ በዕቅድ የሚመራ ያልነበረ ሲሆን አሁን ግን የአስር ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ነድፎ ወረዳ ቤተ ክህነትና አጥብያዎች ድረስ በማውረድ ሥራዎችን በዕቅድ መነሻነት እያከናወነ ይገኛል። በጌዴኦ በኮሬና በቡርጂ ዞኖች በአከባቢው ቋንቋዎች ወንጌልን ለማድረስ ዕቅድ ይዞ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ በሀገረ ስብከቱ የቋንቋ ትርጉም ሥራዎችን የሚሠራ ክፍል ተቋቁሟል። ነገር ግን ከሥራው ስፋት የተነሳ ያለው የገንዘብ እና የሰው ኃይል በቂ አይደለም። ​በአጠቃላይ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት አሁን ላይ ያለው መዋቅራዊ እድገት ጥሩ ቢሆንም፣ ከላይ የተጠቀሱት ተግዳሮቶች የምዕመናን ቁጥር፣ የተጠናከረ መንፈሳዊ አገልግሎት፣ ጠንካራ አስተዳደራዊ መዋቅር በሚፈለገው ልክ እንዳይሆን እንቅፋት ሆነዋል። ​ሀገረ ስብከቱ እነዚህን ችግሮች በመለየትና ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት፣ ወንጌልን በማስፋፋት፣ ወደፊት የተሻለ መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠትና የምዕመናን ቁጥርን ለማሳደግ በሂደት ላይ ያለ ተቋም ነው።

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት Read More »

ጾመ ፍልሰታ/ጾመ ማርያም/

ፍልሰታ ማለት ፈለሰ፤ተሰደደ፤ተጓዘ፤ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሄደ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲሆን ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ «ፈለሰት ማርያም እምዘይበሊ ኀበኢይበሊ፤ ድንግል ማርያም ከሚያልፈው ዓለም ወደማያልፈው ዓለም፣ ከምድር ሕይወት ወደ ሰማያዊ ሕይወት፣ ተሻገረች» በማለት ፍልሰታ የሚለውን ቃል ትርጓሜ አመሥጥሮ ገልጾታል፡፡ ጾመ ፍልሰታ ከእመቤታችን ድንግል ማርያም የዕረፍት ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ እመቤታችን በዚህ ዓለም ፷፬ ዓመታትን በሕይወተ ሥጋ ከቆየች በኋላ ጌታችን የእናቱን ተድላ ነፍሷን እንጂ ተድላ ሥጋዋን አይወድምና ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓመተ ምሕርት አረፈች፡፡ ዕረፍቷም እንደሌላው ሰው በሕማምና በድካም አይደለም፡፡ በገነት ዕፀዋት መዓዛ ተመስጣ ቅድስት ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይታለች፡፡ ታሪኩ በነገረ ማርያም እንደተጻፈው ሐዋርያት እመቤታችንን በአጎበር አድርገው አክብረው ወደጌቴሴማኒ መካነ መቃብር ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉም ነበርና ቀድሞ ልጇን ተነሣ ዐረገ እያሉ ሲያውኩ ኖረዋል፤ እርሷን ደግሞ ተነሣች ዐረገች እያሉ ሊያውኩን ነውና «ኑ የማርያምን ሥጋ በእሳት እናቃጥለው» ብለው በምቀኝነት ተነሱ፡፡ ከመካከላቸው አንድ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ከሐዋርያት እጅ ለመንጠቅ ዘሎ ሄዶ የአልጋውን ሸንኮር ሲይዝ የታዘዘ መልአክ በረቂቅ ሰይፉ እጆቹን ቆረጠው፡፡ እጆቹም በአልጋው ሸንኮር ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ የምሕረት እናት የሆነችው ድንግል ማርያም ቅዱስ ጴጥሮስ ጸልዮ እጆቹን እንዲመልስለት ነግራው እንደነበረ አድርጎለታል፡፡ የእመቤታችን ሥጋዋን መላእክት ከዮሐንስ ወንጌላዊ ጋር በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር ወስደው አስቀምጠውታል፡፡ ሥጋዋ ያለበትን ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ አይቶ እነርሱ ባለማየታቸው እመቤታችን ባረፈች በ፮ኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን እስከ ፲፬ ቀን ድረስ ከጾሙ በኋላ በ፲፬ኛው ቀን ሥጋዋን እንደገና ከጌታ ተቀብለው በጌቴሴማኒ ባለው መቃብር ቀብረውታል፡፡ ከዚህ በኋላ እንደ ልጇ በ፫ኛው ቀን ተነሥታ መላእክት እየዘመሩላት ወደሰማያት ስታርግ፤ ሐዋርያው ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለሰ ዕርገቷን በማየቱ መላእክት «እመቤትህ እርሷ ናት፤ስገድላት» አሉት፤ እርሱም «ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ ይላል፤ከደመናው ሊወድቅ ወደደ» ምክንያቱም ቀድሞ የልጇን ትንሣኤ፤ዛሬ ደግሞ የእርሷን ትንሣኤ ለማየት ብሎ ነው፡፡ እመቤታችንም «ትንሣኤየን ያየህ አንተ ነህ ሌሎቹ አላዩም» ብላ ሐዋርያት ገንዘው የቀበሩበትን የሐር ግምጃ ሰጥታ አጽናንታ ሰደደችው፡፡ ቅዱስ ቶማስ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የእመቤታችን ነገር እንዴት ሆነ ብሎ ጠየቃቸው፤እነርሱም አግኝተው እንደቀበሯት ነገሩት፤ እርሱም ያየውን ምሥጢር በልቡ ይዞ «ሞት በጥር፤ በነሐሴ መቃብር፤ ለሰሚውም አያምር፤ይህ እንዴት ይሆናል?»፤ ቢላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ «ድሮም አንተ ተጠራጣሪ ነህ፤ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይናገር የነበረ እንዲሉ፤ ገንዘን የቀበረን እኛ እያለን እንዴት ትጠራጠራለህ» ብለው ወደ መቃብሯ ሄደው መቃብሯን ቢከፍቱት ባዶ ሆኖ አገኙት፡፡ በዚህ ተደናግጠው ተያዩ፤ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችን ተነሣች፤ዐረገች፤ ይኸው ምልክቱ» ብሎ ገንዘው የቀበሩበትን ሰበን አሳያቸው፤እነርሱም አምነው ሰበኗን ለበረከት ተካፈሉት፡፡ በዓመቱ ነሐሴ ፩ ቀን ሐዋርያት በመንፈሰዊ ቅናት ተነሳስተው «ቶማስ ትንሣኤዋን አይቶ እኛ ሳናይ እንዴት ይቀርብናል» በማለት ነሐሴ ፩ ቀን ሱባኤ ጀምረው በ፲፮ኛው ቀን የሐዋርያትን ሱባኤ ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር ጴጥሮስን ተራዳኢ፣ ካህን እስጢፋኖስን ሠራዔ ዲያቆን አድርጉ ቀድሶ አቅርቧቸዋል፡፡ ከዚያ ጊዜ በኋላም ከነሐሴ ፩ እስከ ፲፭ ቀን ጾመ ፍልሰታ ተብሎ ሁሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ ይጾመዋል፡፡ የጾሙና የትንሣኤዋ በረከት ተካፋይ ያድረገን፤አሜን።

ጾመ ፍልሰታ/ጾመ ማርያም/ Read More »

የአባ ገሪማ መልዕክት  

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ አሜን! በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት፤ በሀገር ውስጥና በመላው ክፍላተ ዓለም የምትገኙ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምዕመናን ወምዕመናት በቸርነቱ እና በረድዔቱ ብዛት በዕድሜያችን ላይ ይህችን ዓመት ጨምሮ ለ2017 ዓ.ም ለጾመ ማርያም እንኳን በሰላም አደረሳችሁ! ጾመ ፍልሰታ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከ፯ የአዋጅ አጽዋማት መካከል አንዱ ነው። ቅዱሳን ሐዋርያት ከእመቤታችን መለየታቸው እጅግ አሳዝኗቸው በነበረበት ጊዜ የጾሙት ጾም ነው። በጾማቸው እመቤታችንን አግኝተውበታል። ውድ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ጾመ ፍልሰታ ሕጻኑም አረጋዊውም ጠንካራውም ደካማውም ወንዱም ሴቱም ሁሉም የሚጾሙት ጾም እንደሆነና ከሌላው ጊዜ በተለየ የሱባኤ ወቅት መሆኑ ይታወቃል። ይኸውም ምዕመናን በጾሙ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድዔት በረከት እንደሚገኝበት እመቤታችን የልባችንን መሻት እንድትፈጽምልን የምንማጸንበት ወቅት መሆኑን በመረዳት ነው። “ጾም ቅድስት ትሜህሮሙ ለወራዙት ጽሙና ዛቲ ጾም ቅድስት ወበይእቲ ጾም ተመጠወ ሙሴ ሕገ እግዚአብሔር ጾም ቅድስት ወበይእቲ ጾም ኤልያስ ዓርገ ውስተ ሰማያት ጾም ቅድስት ወበይእቲ ጾም ዳንኤል ድኅነ እምአፈ አናብስት ጾም ቅድስት ሶስና ድኅነት እምዕደ ረበናት ጾም ቅድስት ዓቀመ ኢያሱ ፀሐየ በገባዖን ጾም ቅድስት ጳውሉስኒ ይቤ ትግሁ እንከ አኃውየ በጾም ወበጸሎት ዛቲ ጾም ቅድስት ወበይእቲ ጾም ጾም ቅድስት ትሚህሮሙ ለወራዙት ጽሙና። ቅድስት ጾም ለወጣቶች እርጋታ ዝምታን ታስተምራቸዋለች፡፡ ጾም የተለየችና የተቀደሰች ናት በዚህች የተቀደሰችዋ ጾም ሙሴ የአምላኩን ሕግ ተቀበለባት፤ ጾም የተለየችና የተቀደሰች ናት:  በዚህች ቅድስት ጾም ኤልያስ ወደ ሰማይ ዐረገባት በዚህች ቅድስት ጾም ዳንኤል ከአንበሶች አፍ ዳነባት፣ ጾም የተለየችና የተቀደሰች ናት:: በዚህች ቅድስት ጾም ሶስና ከመምህራኑ ክስ ተርፋለች፣ በዚህች ቅድስት ጾም ኢያሱ በገባዖን ፀሐይን አቆመ ። ጾም የተለየችና የተቀደሰች ናት! ጳውሎስ እንዲህ አለ “እንግዲህ ወንደረሞቼ በጾምና በጸሎት ትጉ”፣ ጾም የተለየችና የተቀደሰች ናት። በዚህች በተቀደሰችዋ ጾም … ቅድስት ጾም ለወጣቶች እርጋታ ዝምታን ታስተምራቸዋለች” እንዳለ ቅዱስ ያሬድ የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ፍትሐ ነገስት በአንቀጽ 15፣598 ላይ “ወአኮ ጾም እምኀብስት ወማይ አላ ጾምሰ ዘውኩፍ ቅድመ እግዚአብሔር ንጽሐ ልብ – ጾም ከእህል ከውሃ መከልከል ብቻ አይደለም እግዚአብሔር የሚቀበለው ጾም የልብ ንጸሕና ናት” እንደሚለን እኛም ይህንን ጾም ጾመን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድዔት በረከት ለማግኘት የልብ ንጽህናን ገንዘብ ማድረግ ዋናው ቅድመ ሁኔታ ነው። በዚህ ጾም በቤተ ክርስቲያናችን በተለየ መልኩ ሶርያዊ ለብሐዊ የተባለ ቅዱስ ኤፍሬም የደረሰው የእመቤታችን ውዳሴዋ (ውዳሴ ማርያም) እንዲሁም የብሕንሳው ኤጴስ ቆፅስ አባ ሕርያቆስ የደረሰው የእመቤታችን ቅዳሴ (ቅዳሴ ማርያም) ይተረጎማል። በዚህ ጊዜ እንዲሁም በሌሎቹም በቤተ ክርስቲያን በሚሰጡ መንፈሳዊ አገልግሉቶች በሰዓታት፤ በኪዳን፤ በቅዳሴ፤- በሚሰጠው  የስብከተ- ወንጌል አገልግሎት ላይ እየተገኘን አገልግሎቱን እየተሳተፍን ቸሩ አምላካችን ለሀገራችን ለኢትዮጵያና ለሕዝቦቿ ፍጹም ሰላምን እንዲሰጣት እና ከእመቤታችን በረከት ረድዔት እንዲያሳትፈን ልንጸልይ ይገባል እያልን አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን። በመጨረሻም በቅድስና በንጽሕና በተሰበረ ልብ ሆነን ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት፤ የልቡናችን መልካም መሻት የሚፈጸምበት፤ ኃይለ አጋንንት ወድቆልን ኃይለ መንፈስ ቅዱስ የሚቀርብን የበረከት ጾም ያድርግልን። ጾሙን የሰላም የፍቅር የበረከት ጾም አምሳካችን ልዑል እግዚአብሔር ያድርግልን። እግዚአብሔር ሀገራችንን ይባርክልን!!! አባ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስ

የአባ ገሪማ መልዕክት   Read More »

ለገጠር አብያተክርስቲያናት የንዋየ ቅድሳት ድጋፍ ተደረገ!!

በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ለሚገኙ፦ #ለቡርጂ ወረዳ ቤተክህነት #ለኮሬ ወረዳ ቤተክህነት #ለቡሌና ረጴ ወረዳ ቤተክህነት #ለይርጋጨፌ ወረዳ ቤተክህነት ለሚገኙ ገጠር አብያተክርስቲያናት የሚሆን የተለያዩ ንዋየ ቅድሳት መቀደሻ አልባሳት፣ ዣንጥላ፣ ዕጣን፣ ጧፍ ፣ቅዱሳት መጽሐፍት፣ መጎናጸፊያ ፣መጋረጃ፣ ጽና፣ መስቀል ፣ጽዋ ለአራቱም ወረዳ ቤተክህነት ኃላፊዎች ከሀገረ ስብከቱ የሰበካ ጉባኤና የሰ/ት/ቤት ማደራጃ ክፍል ኃላፊ ከመልአከ ብርሃን ዳንኤል ነቢዩ ተረክበዋል። የየወረዳ ኃላፊዎችም የተረከቡትን ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው አብያተክርስቲያናት የሚያደርሱ ይሆናል። በቀጣይም በሀገረ ስብከቱ ለሚገኙ ገጠር አብያተክርስቲያናት የሚያስፈልጉ ንዋየ ቅድሳትን ለማሟላት ድጋፋችሁ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እንጠይቃለን ።

ለገጠር አብያተክርስቲያናት የንዋየ ቅድሳት ድጋፍ ተደረገ!! Read More »

ስድስተኛው ዙር የወጣቶች መርሃግብር ብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ በተገኙበት ተካሄደ!!

በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በዲላ ከተማ በብፁዕ አቡነ ገሪማ በሀገረ ስብከቱ ጳጳስና በቅዱስ ሲኖዶስ አባል የሚመራው ወርሃዊው የወጣቶች መርሃግብር ስድስተኛ ዙር ብፁዕነታቸው በተገኙበት ተካሂዷል። መርሃግብሩ የተመራው መምህር በላይ ሁንደራ ሲሆን ዝማሬ በዘማሪት ሰላም ዘሪሁን እና በዘማሪት ሰላም ሀብታሙ ቀርቧል። እንዲሁም በወጣት ኪሩቤል አሰፋ እና በወጣት እርቅይሁን ደመላሽ ግጥም ቀርቧል። መጋቤ ሀዲስ መልአክ አማረ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔዓለም ካቴድራል የመጻሕፍት መምህር ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ በጻፈው በሁለተኛው መልእክቱ ፪ኛ ጢሞ ፫፥፲፬ ላይ የሚገኘውን “አንተ ግን በተማርህበትና በተረዳህበት ነገር ጸንተህ ኑር ከማን እንደተማርኸው ታውቃለህና” የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ ወጣቶች ውሏቸውን ማስተካከል እንዳለባቸው፣ በቤተ ክርስቲያን በተማሩበት ትምህርት በአሚነ ሥላሴ ጸንተው መኖር እንዳለባቸው በሰፊው አስተምረዋል። በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ ወጣቶቹ ወደዚህ መርሃግብር (ወደ ቤተ ክርስቲያን) ሲመጡ ሌሎቹንም በመጋበዝ፣ ወጣቶች በማይመጥናቸው በአልባሌ ሥፍራ ላይ መገኘት እንደሌለባቸው እንዲሁም ራሳቸውን ከሱስ መጠበቅ እንዳለባቸው ገልጸው ስለሱስ አስከፊነት በሰፊው ተናግረው በቀጣይ ሊሰሩ ስለሚገባቸው ጉዳዮች አባታዊ መመሪያ ሰጥተው መርሃግብሩን በጸሎት ፈጽመዋል። የሚቀጥለው ወር የሚውለው ነሐሴ 25/2017 ዓ.ም ነው።

ስድስተኛው ዙር የወጣቶች መርሃግብር ብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ በተገኙበት ተካሄደ!! Read More »

ለስምንት ወራት የተማሩ ደቀመዛሙርት በብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ ተመረቁ!!

በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በሀገረ ስብከቱ በተቋቋመው በአንዲዳ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን የተማሩ የአብነት እና የተለያዩ መሠረታዊ ትምህርትና ሥልጠና የወሰዱ ከ5ት ወረዳ ቤተክህነት የተወጣጡ 5ት ደቀመዛሙርት በብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተመረቁ። በምርቃ መርሐ ግብር ከፍተኛ ውጤት ያመጡ ደቀመዛሙርት የተሸለሙ ሲሆን የተለያዩ መጻሕፍት ከማህበረ ቅዱሳን ተሰጥቷቸዋል።በተጨማሪ ያለ ምንም ክፍያ ለስምንት ወራት ያስተማሩ መምህራን በብፁዕነታቸው ተመስግነዋል ሽልማት ተሰጥቷቸዋል። የደብረ ሰላም ቅዱስ ዑራኤል ቤተክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት መዘምራን መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን ተመራቂ ደቀመዛሙርትም ያሬዳዊ ወረብና ግጥም አቅርበዋል ። ስለ ተመራቂ ደቀመዛሙርት አጠቃላይ ቆይታ በቀሲስ ጤናው እንዳለማው ቀርቧል። አጠቃላይ አጭር ስለ አብነት ት/ቤቱ ሪፖርት በመልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ዮሐንስ ምሕረቱ የሀገረ ስብከቱ የትምህርትና የካህናት አገልግሎት ክፍል ኃላፊ ገልጸዋል ። በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ቃለምዕዳን ያስተላለፉ ሲሆን ደቀመዛሙርት የተሰጣቸውን ተልዕኮ መወጣት ማስተማር እንዳለባቸው አሳስበዋል ።

ለስምንት ወራት የተማሩ ደቀመዛሙርት በብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ ተመረቁ!! Read More »

ሊቀ ስዩማን ቀሲስ ምህረቴ ገ/ሥላሴ የሻራ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ እንዲሆኑ በብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬ ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተሹመዋል።

በዕለቱም የማስተዋወቅ መርሐ ግብሩን ያከናወኑት የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ በሆኑት በመልአከ ብርሃን ቀሲስ አጥናፉ ማሞ የማስተዋወቅ ሥራ ተከናውኗል። በመጨረሻም በሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ በመልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ መልካም የሥራና የአገልግሎት ዘመን እንዲሆንላቸው በመመኘት በጸሎት ተፈጽሟል።

ሊቀ ስዩማን ቀሲስ ምህረቴ ገ/ሥላሴ የሻራ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ እንዲሆኑ በብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬ ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተሹመዋል። Read More »

በግንባታ ላይ የሚገኘው የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ ጉብኝት ተደረገ!!

የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት የሀገረ ስብከት አቀፍ ጠቅላላ ጉባኤ ተሳታፊዎች አዲስ ሀገረ ስብከቱ በዲላ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ የሚያስገነባውን የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ ጉብኝት አደረጉ። በጉብኝቱ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ፣ የሀገረ ስብከቱ የየክፍል ኃላፊዎች፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆች እና ጸሐፊዎች፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎችና ጸሐፊዎች በጠቅላላ ጉባኤው የተገኙ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። በጉብኝት ስለሕንጻው አሁናዊ ሁኔታ ገለጻ የሰጡት ኢንጅነር አማኑኤል ሲሆኑ ሕንጻው በደረሰበት ደረጃ መደነቃቸውን ተሳታፊዎቹ ገልጸዋል። በተጨማሪ በቅጥር ግቢ ውስጥ እየተሰሩ የሚገኙት የግብርና የልማት ሥራዎች የተጎበኙ ሲሆን ብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ ወደፊት ስለሚሰሩ ሥራዎች ገለጻ አድርገው እንዲሁም ለመጎብኘት ለመጡት እንግዶች ምስጋና አቅርበው ፍጻሜ ሆኗል።

በግንባታ ላይ የሚገኘው የመንበረ ጵጵስና ሕንጻ ጉብኝት ተደረገ!! Read More »

Scroll to Top