በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት

Uncategorized

ብፁዕ አቡነ ገሪማ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት ያስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት!

ኤክቱስ ጥር 10/2018 ዓ.ም በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። በሀገረ ስብከታችን፣ በሀገር ውስጥና በሌሎች ክፍላተ ዓለም የምትገኙ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናን ወምእመናት፤ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ድኅነተ ዓለም ሲል በባሕረ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ ለተጠመቀበት፣ ለታላቁ የአደባባይ በዓላችን ለብርሃነ ጥምቀቱ እንኳን በሰላም አደረሳችሁ! “ርእዩከ ማያት እግዚኦ ርእዩከ ማያት ወፈርሁ  ደንገፁ ቀላያተ ማያት ወድምጸ ማያቲሆሙ – አቤቱ ውኃዎች አዩህ ውኃዎችም አዩህና ፈሩ ጥልቆችም ተነዋወጡ ውኃዎችም ጮሁ።” መዝ. ፸፮፥፲፮ ይህ የቅዱስ ዳዊት ቃለ ትንቢት ባሕርየ ሰብእን ለማዳን በተዋሕዶ ሰው የሆነው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ ሊጠመቅ በቆመ ጊዜ ግዑዛን ፍጥረታት ፈጣሪያቸውን አውቀው ያሳዩትን ድንጋጤ የሚገልጽ ነው። ጌታችን ወደ ዮርዳኖስ ለመጠመቅ የሄደው መጠመቅ የሚገባው ሆኖ ሳይሆን፣ እርሱ ማየ ሕይወት በመሆኑ “አፍላገ ማየ ሕይወት ዘይውኅዝ እምከርሡ – ከሆዱ የሕይወት ውኃ ወንዝ ይፈስሳል” (ዮሐ. ፯፥፴፰) ተብሎ እንደተጻፈ፤ ውኃውን ቀድሶ ለእኛ የልጅነት መገኛ እንዲሆንልን ነው። በዚያን ዕለት ዮርዳኖስ ወደ ኋላ የሸሸውና ጥልቆች የተነዋወጡት፣ በማዕከለ ዮርዳኖስ የቆመውን የጌታችንን የባሕርይ አምላክነት ተረድተው ነው። ይህ ምስጢርም “ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኅሬሁ – ባሕር አየችና ሸሸች፤ ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ” (መዝ. ፻፲፫፥፫) ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተመሰከረ፣ የሰው ልጅ የኃጢአት ዕዳ ተደምስሶ ከጨለማ ወደ ብርሃን የተሸጋገረበት ታላቅ የድል ቀን ነው። የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤ ጌታችን በዮርዳኖስ የተጠመቀው ለእኛ የድኅነትን መንገድ ሊከፍትልንና በጥምቀቱ የኃጢአት ዕዳችንን ደምስሶ አዲስ ሕይወትን ሊሰጠን ነው። በመሆኑም ይህን ታላቅ የድኅነት በዓል ስናከብር ክርስቶስ የከፈለንን ዋጋ እያሰብንና በጥምቀት ካገኘነው ልጅነት ጋር በሚስማማ ክርስቲያናዊ ሥነ-ምግባር ሊሆን ይገባል። በጥምቀት ያገኘነውን ልጅነት ከሚጋርዱ፣ ከቤተ ክርስቲያን ጥንታዊ ሥርዓት ውጭ ከሆኑና የምስጢረ ጥምቀቱን ረቂቅነት ከሚያደበዝዙ ሥጋዊ ድርጊቶች ተቆጥበን፤ በዓሉን በሥርዓተ አምልኮ፣ በጸሎት እና መልካም ሥራዎችን በመሥራት  ልናከብረው ይገባል።  በመጨረሻም፣ ይህ የ፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት የጥምቀት በዓል አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ የሰጠንን የልጅነት ጸጋ በሃይማኖትና በምግባር አጽንተን እንድንኖር ይርዳን። በማዕከለ ዮርዳኖስ የቆመው የባሕርይ አምላክ ለሀገራችን ሰላምን፣ ለሕዝባችንም ጤናንና በረከትን ያድልልን። እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ! አባ ገሪማየጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል

ብፁዕ አቡነ ገሪማ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት ያስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት! Read More »

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በሀገረ ስብከቱ የሚሠሩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ!

ኤክቱስ ጥር 6/2018 ዓ.ም ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት የቅዱስ ሲኖዶስ አባል እና ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት የሚሠሩ በርካታ የልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ሀገረ ስብከቱ በዲላ ከተማ የሚያስገነባው የመንበረ ጵጵስና ግንባታ፣ በዲላ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የሚሠራው የውኃ እና የዶሮ ልማቶች ተጎብኝተዋል። በተጨማሪም በአንዲዳ የሚገኘው የአዳሪ የአብነት ትምህርት ቤት መደበኛ የመማር የማስተማር ሂደት፣ አዲስ ለመገንባት የታሰበበት ቦታ፣ የተማሪዎች የማደርያና የመመገቢያ ክፍላት እንዲሁም የአብነት ትምህርት ቤቱ ጽሕፈት ቤት ተጎብኝቷል። ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስ በአጠቃላይ ስለሚሠሩ የልማት ሥራዎች ገለጻ ያደረጉ ሲሆን ብፁዕነታቸው በሀገረ ስብከቱ የተሠሩ ሥራዎችን እና ደቀ መዛሙርቱን በመጎብኘታቸው እና ቡራኬ በመስጠታቸው እጅግ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸው ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ሊቀ ጳጳስ በተመለከቱት ሥራዎች ፍጥነት መገረማቸውን የገለጹ ሲሆን ሁሉም አካል ከብፁዕነታቸው አጠገብ ከሆነ ከዚህ በላይ በርካታ ሥራዎችን በሀገረ ስብከታቸው እንደሚሠሩና ገና ብዙ ያልተጠቀምንባቸው አባት መሆናቸውን ገልጸው እግዚአብሔር ሀገረ ስብከቱን በፍጹም ሰላም እንዲጠብቅ በመማጸን ጉብኝታቸውን በጸሎት ፈጽመዋል። በመርሃግብሩ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሕይወት ብርሃኑ ክፍሌን ጨምሮ የክፍል ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በሀገረ ስብከቱ የሚሠሩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ! Read More »

የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ (ፍቁረ እግዚእ) ዓመታዊ በዓል በዲላ ማረሚያ ተቋም ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ተከበረ!

ኤክቱስ ጥር 4/2018 ዓ.ም በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በመንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት ስር በሚገኘው የዲላ ማረሚያ ተቋም የፍቁረ እግዚእ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሱ ዓመታዊ የፍልሰቱ መታሰቢያ በዓል ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል በተገኙበት ተከብሮ ውሏል። በዲላ ከተማ የሚገኙ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በሥፍራው ተገኝተው የዕለቱን በዓል የሚገልጽ ያሬዳዊ ወረብ አቅርበዋል። ይህ በማረሚያ ተቋሙ ውስጥ የሚገኘው የፍቁረ እግዚእ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ለታራሚዎች መንፈሳዊ አገልግሎት ከመስጠት ባለፈ በሥነ-ልቦና ጥንካሬ እና በሥነ-ምግባር ታንጸው እንዲወጡ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ እንደሚገኝ የሀገረ ስብከቱ የምግባረ ሰናይ ክፍል ኃላፊ መምህር በየነ ክፍሌ ገልጸዋል። በዕለቱ ብፁዕነታቸው ለታራሚዎች እና ለበዓሉ ታዳሚዎች የዕለቱን ትምህርት አስተምረዋል። ብፁዕነታቸው በትምህርታቸው የቅዱስ ዮሐንስን የፍቅርና የጽናት ሕይወት መነሻ በማድረግ፣ ታራሚዎች በማረሚያ ቆይታቸው በሥነ-ምግባር ታንጸው ለተሻለ ሕይወት እንዲዘጋጁ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል። በተጨማሪም የሕግ ታራሚዎቹ በማረሚያ ቤት ውስጥ የሚያሳልፉት ጥቂት ጊዜ ብቻ መሆኑን በመግለጽ ከዚህ በላይ ግን ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ ከዘለዓለም እስራት ነጻ መውጣት እንደሚገባ በመግለጽ መርሃ-ግብሩን በጸሎት አጠናቅቀዋል።

የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ (ፍቁረ እግዚእ) ዓመታዊ በዓል በዲላ ማረሚያ ተቋም ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ተከበረ! Read More »

እመኬ ፈቀድኩ የሀሉ እስከ ሶበ እመጽእ ሚ ላዕሌከ(እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ ምን አግዶህ?) ዮሐ ፳፩ ፥ ፳፪

ጥር ፬ ቀን ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ከዚህ ዓለም የተሰወረበት ዕለት ነው ።የቅዱስ ዮሐንስን መሰወር ከመናገራችን በፊት ቅዱስ  ዮሐንስ ወንጌላዊ ማን ነው ?ምን ምን አደረገ የሚሉትን ነጥቦች በአጭር እንመልክት።ቤተሰቦቹ፦ የቅዱስ ዮሐንስ አባቱ ዘብዴዎስ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል ማቴ 4፥21 እናቱንም የዘብዴዎስ ልጆች እናት በማለት ስሟን ሳይጠራ ይገልጣታል። ማቴ 27፥56 20፥22 የትርጓሜ ሊቃውንት ግን ማርያም ባውፍልያ ናት በማለት ገለጠዋታል።ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንሰ ክርስቶስን ከመከተሉ በፌት    የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ደቀ መዝሙር ነበር። ዮሐንስ መጥምቅ እነሆ የእግዚአብሔር  በግ ብሎ ሲያስተምር ሰምተው ክርስቶስን ከተከተሉት ከሁለቱ ደቀመዛሙርት ስሙ ያልተጠቀሰው  አንዱ ዮሐንስ ወንጌላዊ ነው ዮሐ 1፥35-41። ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ለሐዋርያነት የተጠራው ከአባቱና ከወንድሙ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ ሲያጠምድ ነው ።እነርሱም ከወንድሙ ጋር ዓሣ የሚያጠምዱበትን መረብ እና አባታቸውን በመተው ክርስቶስን እንደተከተሉት በመጽሐፍ ቅድስ ተመዝገቧል ማቴ 4፥21 ክርስቶስን ለመከተል ዓለማዊ ነገርን ሁሉ ትቶ መከተል እንደሚገባ የተማርነው ከሐዋርያት ነው ። ክርስቶስን ለመከተል መረብን(ወጥመድን) መተው ያስፈልጋል።አንድ አንድ ጊዜ ዓሣ የምናሠግርበት መረብ እኛን የሚያሠግርበት አጋጣሚ ይፈጠራል ስለዚህ  መረብን መተው ክርስቶስን ለመከተል ቁልፍ ጉዳይ ነው ። መረብ ለዓሣ አሥጋሪ የኑሮ መሠረትና  ሀብት ነው ። ዮሐንስ ግን ዘለዓለማዊውን ሀብት ክርስቶስን ለማግኘት ጊዜያዊውን ሀብት መረቡን ትቷል። የዮሐንስ ስሞች፦ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን ከተከተለ በኋላ ብዙ ስሞች ተሰጥተውታል እነርሱም ፦              1 ወልደ ነጎድጓድ ተብሏል              2 ፍቁረ እግዚእ   ተብሏል              3 ቴዎጎሎስ/ታዎጎሎስ ተብሏል              4 አቡቀለምሲስ ተብሏል1ኛ ወልደ ነጎድጓድ ብሎ የሰየመው መድኅነ ዓለም ክርስትስ ነው ። ዮሐንስንና ወንድሙ ያዕቆብን በአኔርጌስ ብሏቸዋል ትርጉሙም  ደቂቀ ነጎድጓድ/የነጎድጓድ ልጆች ማለት ነው ማር 3፥17ይህም  ማለት ደቂቀ ምስጢር ማለት ነው። ይህም ስም ለቅዱስ  ዮሐንስ ይስማማዋል ብዙ ምስጢራት በራዕይ ተገልጠውለታልና።2ኛ ፍቁረ እግዚእ (ጌታ የሚወደው ደቀመዛሙር )  ተብሏል ይህስያሜ በዮሐ 13፥23 ላይ ተመዝግቧል ። ጌታ የሚወደው መባሉም ከሌሎች ደቀ መዛሙርቱ አብልጦ ይወደው ስለነበረ ነው። ከሌሎች በተለየ የዮሐንስ መወደዱ ዮሐንስ በእምነቱ ጠንካራ ስለነበረ ነው።ጌታችን በተሰቀለ ጊዜ ከመስቀሉ ሥር የተገኘ ዮሐንስ ብቻ ነውና ዮሐ19፥26 በዚህም  በእምነቱ ምን ያህል  ጠንካራ እንደሆነ እንረዳለን።  3 ቴዎሎጎስ /ታዎሎጎስ ተብሏል። ነባቤ መለኮት ማለት ነው  ይህም ማለት የአምላክን የመለኮትን ነገር የተናገረ ማለት ነው ። ዮሐንስ ነባቤ መለኮት የተባለበት ምክንያት «በመጀመርያ ቃል ነበረ » ዮሐ1፥1በማለት የወልድን መለኮታዊ ህልውና፣የወልድን ቀዳማዊነት እና የዓለማት ሁሉ ፈጣሪ መሆኑን ስለ ተናገረ ነው።4 አቡቀለምሲስ ይባላል ።አቡቀለምሲስ የጽርዕ ቃል ነው። በግእዝ አበ ራዕይ አበ ትንቢት ማለት ሲሆን በአማርኛ ደግሞ ባለ ትንቢት የትንቢት ባለቤት ባለ ራዕይ የራዕይ ባለቤት ማለት ነው ።ሁለተኛው ትርጉም ረዐየ ኅቡአት/የተሰወሩ ነገሮችን የሚያይ ማለት ነው ። ዮሐንስ በልዩ ልዩ ፀጋዎች የደመቀ ሐዋርያ ነው ።ፀጋውም፦ ንጽሕና ፣ ቅድስና እና ድንግልና ናቸው።እንደ ዮሐንስ ስለ ንጽሕና የተነገረለት ሐዋርያ የለም።ቅዱስ ያሬድ ዮሐንስን ስለ ንጽሕናው እንዲህ  ይገልጠዋል፦ ለትጉሓን ይኤምሮሙ እስመ ኀብረ ንጽሐ ምሥሌሆሙ ዮሐንስ ክቡር ሰባኬ ወንጌል መምህር ወድንግል /ወንጌልን የሚሰብክ ክቡር መምህር ዮሐንስን መላእክትን ይመለከታቸዋል ፤ በንጽሕና ከእነርሱ ጋር አንድ ሆኗልና በማለት የዮሐንስን  ንጽህና ይገልጠዋል።/ድጓ ገጽ 191/ሀገረ ስብከቱ፦ ሐዋርያት ጌታ ካረገ በኋላ መንፈስ ቅዱስንም ከተቀበሉ በኋላ ይህን  ዓለም  በዕጣ ተካፍለው ለስብከተ ወንጌል ወጥተዋል።ዕጣ በሚጣጣሉበትም ጊዜ ምድረ ጽርዕ /ግሪክ/ለቅዱስ ዮሐንስ ደርሳዋለች። በምድረ ጽርዕ በኤፌሶን አርጤምስ የምትባል ጣዖት ትመለክ ነበር። ዮሐንስ ሰው በሚመለከት ሀገር አልሄድም ብሎ ነበርና ቅዱስ ጴጥሮስ አጽናንቶ ወስዶ አድርሶት ተመልሷል።እንዲህ ሆኖ ቢሄድም ቅሉ ወንጌልን ለማስተማር ምቹ ሁኔታ ባለማግኘቱ ምክንያት ከደቀ መዝሙሩ ከአብሮኮሮስ ጋር በመመካከር ከአንዲት ሮምና ከምትባል ሴት ቤት አግልጋይ በመሆን ገቡ።ዮሐንስ ለውሽባ ቤት እሳት  አንዳጅ ሆነ።ደቀመዝሙሩ አብሮኮሮስም አጣቢ/ጽዳተኛ/ሆነ።ሮምናን በተአምራት /የሞተውን  ልጅ በማስነሳት/አሳምነው አግልግሎታቸውን ጀምረዋል።በጣም የሚገርመኝ ግን ፦ አባቶቻችን ሐዋርያት የክርስቶስን ወንጌል ለዓለም ለማዳረስ ብዙ ዓይነት መንገዶችን ተጠቅመዋል  የጽዳት ሰራተኛ በመሆን ፣ከሕመምተኞች ጋር ሕመምተኛ  በመሆን ፣የውሽባ ቤት እሳት አንዳጅ በመሆን…አስተምረዋል። የእኛ ዘመን ሐዋርያት ግን ይገርሙኛል ለ3 ቅን አገልግሎት 50እና 60 ሺህ ብር ይጠይቃሉ የሚገርም ነው! ይህም እንኳ ተከፍሏቸው  በሰዓት  ቢገኙ መልካም ነበር። ምን አልባት እነ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ የሰባኪዎችን ሁኔታ በአካለ ስጋ ቢያዩት ምን ይሉ ይሆን! ቅዱስ ዮሐንስ ግን የክርስቶስን ወንጌል ያስተማረ የቤት ሰራተኛ በመሆን ነበር። ያውም የሞተውን  ልጅ አስነስቶ  ቅድስናው እስኪታወቅ ድረስ በመገፋትና በመለጋት ነበር። ይህን ድንቅ ተአምር ከፈጸመ  በኋላ ግን ሮምናን ከነቤተሰቦቿ  የክርስቶስን  ልጅነት እንድታገኝ አስተምሯታል። በኋላም ከንጉሡ ጀምሮ እስከ ሕዝቡ ድረስ በክርስቶስ አምነው ተጠምቀዋል።ቅዱስ ዮሐንስም ወንጌልን እያስተማረ ብዙ ድንቅድንቅ ተአምራትን አያደረገ ብዙ ዘመን  ኑሯል ። ለሕዝቡም               ካህናትን ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ  ወደሌሎች አቅራቢያ ሀገሮች ሄደ።በመጨረሻም በከሀዲውና በጨካኙ ንጉሥ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ ። በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋላ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት ።በዚያም ሳለ ራዕዩን አይቶ ጻፈው ።ክፉዎች  ያሰቃየነው ቢመስላቸውም እግዚአብሔር ግን ለራዕይ ተስማሚ የሆነ ቦታ አዘጋጅቶለት ነበር!ድምጥያኖስ ከሞተ በኋላ ከግዞት ተመልሶ ወንጌሉንና ሶስቱን መልእክታቱን ጽፋል።እግዚአብሔር ሙት ያላለውን መግደል ስለማይቻል ከሳሾቹ ሲሞቱ እንዲሞት የተፈረደበት ቅዱስ ዮሐንስ ግን በሕይወት ወደቦታው ተመልሶ ወንጌልን ያህል  የአምላኩን ቃል ለመጻፍ በቃ።እግዚአብሔር ሲመርጥ ከግዞት ቤት አውጥቶ ሥራ  ያሠራል /ወንጌልን ያጽፋል/። አንዳዱ ደግሞ ከክርስቶስ ወንጌል ወጥቶ  በሉተር ተረት ያብዳል።ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ከማስተማር በተጨማሪ ታዋቂ እና የተዋጣለት ስዕል ሳይ ነበር።የክርስቶስን ስዕለ ስቅለት በመጀመርያ የሳለው እርሱ ነው ።ቅዱስ ዮሐንስ ከሶስቱ  የምስጢር ደቀመዛሙርት አንዱ ነው እናታችን ድንግል ማርያምንም ከመስቀሉ ስር በእናትነት የአዳምን ልጆች ወክሎ የተቀበለ እርሱ ነው ። እንዴት ያስደስታል የሚወዳትን  እናቱን ለሚወደው ደቀመዝሙሩ  ሰጠው ።ለድንግሉ ደቀመዝሙሩ ድንግል እናት ሰጠው።ቅዱስ ዮሐንስ እስከ መጨረሻው መጽናቱ ድንግል ማርያምን በእናትነት ለመቀበል አብቅቶታል ።ዮሐ 19፥26 ክርስቶስ በተሰቀለ ጊዜ ሁሉም ሐዋርያት ሲበተኑ እርሱ ብቻ ቅርቶ ነበርና ነው ። በመጨረሻም ከዚህ ዓለም የሚሰወርበት ጊዜ ሲደርስ 99 ዓም ደቀመዛሙርቱን የመቃብር ገደል አስቆፍሮ ለኤፌሶን ሰዎች በተማራችሁበት ትምህርት  ጸንታችሁ ኑሩ የሚል መልእክት አስተላልፎላቸው ከዚያ ውስጥ ገብቶ ከጸለየ በኋላ እንደ ሄኖክና እንደ ኤልያስ ወደ ብሔረ ሕያዋን ሄዷል።ከላይ በርእሱ እንደተጠቀሰው  አስቀድሞ ጌታ የሐንስ እስከ ዳግም ምጽአት ሞትን እንደማይቀምስ ተናግሮለት ስለ ነበር ሞትን አልቀመሰም። ዮሐንስ ሞትን እንደ ማይቀምስ ሁለት ጊዜ ተናግሯል፦   1እውነት እላችኋለሁ የሰው ልጅ በመንግሥቱ እስኪመጣ ሞትን የማይቀምሱ አሉ ብሎ ነበር ሜቴ16፥28 በዚህ  ንባብ ውስጥ ማን እንደ ማይሞት አልተጠቀሰም ነገር ግን የሞይሞት እንዳለ ተገልጧል።   2 ሁለተኛው እኔ እስክመጣ ቢኖር ምን  አግድህ?ያለው ነው ዮሐ 21፥22 በዚህ ንባብ ውስጥ ደግሞ ዮሐንስ ሞትን እንደማይቀምስ በግልጥ ክርስቶስ አስተሞሯል። ስለዚህ ቅዱስ ዮሐንስ  ወንጌላዊ ሞትን አልቀመሰም።ጥር አራት ቀን ወደ ብሔረ  ሕያዋን ሄዷል።

እመኬ ፈቀድኩ የሀሉ እስከ ሶበ እመጽእ ሚ ላዕሌከ(እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ ምን አግዶህ?) ዮሐ ፳፩ ፥ ፳፪ Read More »

አስራ አንድ የሕግ ታራሚ ኢ-አማንያን በብፁዕ አቡነ ገሪማ ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አገኙ!

ኤክቱስ ጥር 4/2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት በዲላ ማረሚያ ተቋም በሚገኘው በወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ አስራ አንድ የሕግ ታራሚዎች በብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አግኝተዋል። ተጠማቂዎቹ ከዚህ በፊት የቅድመ ጥምቀት መደበኛ ትምህርት የተማሩ መሆናቸውንና አሁን ደግሞ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገረ ኃይማኖት፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን እና ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር እየተማሩ እንደሚገኙ ተገልጿል። በተጨማሪም የሀገረ ስብከቱ የስብከተ ወንጌልና የምግባረ ሰናይ ክፍላት ከመንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት እንዲሁም ከማረሚያ ቤቱ ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ጋር በመተባበር እንደተሠራና ሌሎችም በርካታ ሥራዎች በመሠራት ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል። በመጨረሻም ብፁዕነታቸው ተጠማቂያኑ በኃይማኖት እንዲጸኑና እንዲበረቱ እንዲሁም መንፈሳዊ ትምህርታቸው በሚገባ እንዲከታተሉ አባታዊ ምክራቸውን ለግሰው በጸሎት ፈጽመዋል።

አስራ አንድ የሕግ ታራሚ ኢ-አማንያን በብፁዕ አቡነ ገሪማ ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አገኙ! Read More »

A message transmitted by Hisgrace Abune Gerima Bishop

​A message transmitted by His Eminence Abune Gerima, bishop of the Gedeo, Kore, and Burji Diocese and Member of the Holy Synod, regarding the 2018 E.C. Nativity of Our Lord and Savior Jesus Christ, addressed to his spiritual children within the Gedeo, Kore, and Burji Diocese, across the nation, and in various parts of the world. ​Ichthus: Tahsas 28, 2018 E.C.

A message transmitted by Hisgrace Abune Gerima Bishop Read More »

Eebbisemeek Abune Geriima Gede’o Koorenna Burjixxe Hagere Sibkete Phaaphaasichchi Qullitte Sinoodeesexxi una 2018 G.W Goottanna Qorsa Iyyesuusi Kiristoosika ilenshatika ayyaana uuddaaxxin Qullichchi manfasixxe ila insa’nexxee Gede’uffat Laagadinni Sa’issineexxa erga.

Ekituus Arfaasa 28/2018 G.W

Eebbisemeek Abune Geriima Gede’o Koorenna Burjixxe Hagere Sibkete Phaaphaasichchi Qullitte Sinoodeesexxi una 2018 G.W Goottanna Qorsa Iyyesuusi Kiristoosika ilenshatika ayyaana uuddaaxxin Qullichchi manfasixxe ila insa’nexxee Gede’uffat Laagadinni Sa’issineexxa erga. Read More »

ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የ2018 ዓ.ም የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን በተመለከተ በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት፣ በሀገር ውስጥና በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ለሚገኙ ለመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው ያስተላለፉት መልእክት።

ኤክቱስ ታኅሣሥ 28/2018 ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የ2018 ዓ.ም የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን በተመለከተ በጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት፣ በሀገር ውስጥና በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ለሚገኙ ለመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው ያስተላለፉት መልእክት። Read More »

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ልደቱ ለእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ  ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመት ምሕረት

ኤክቱስ ታኅሣሥ 28/2018 ዓ.ም በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! +  በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣+  ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣+  የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣+  በሕመም ምክንያት በየፀበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣+  እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት በሙሉ፣ እኛ በሕይወት እንኖር ዘንድ አንድ ልጁን ወደ ዓለም የላከ እግዚአብሔር ኣምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዓስራ ስምንት ዓመተ ምሕረት በዓለ ልደቱ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!“ወበዝንቱ ተዓውቀ ፍቅሩ ለእግዚአብሔር ላዕሌነ እስመ ለወልዱ ዋሕድ ፈነዎ ውስተ ዓለም ከመ ንሕየው በእንቲኣሁ፤ ወዝንቱ ውእቱ ፍቅሩ ለእግዚአብሔር፡- የእግዚአብሔር ፍቅሩ በእኛ ዘንድ ተገለጠ፤ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና የእግዚአብሔር ፍቅር ይህ ነው፤ (፩ዮሓ. ፬፥፱) በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው እኛ ምሥራቃውያን ክርስቲያኖች በዛሬው ዕለት የምናከብረው በዓል፣ የጌታችን የኣምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ነው፤ በዓለ ልደት የእግዚአብሔር ሰላምና ፍቅር ለሰው ልጆች ሁሉ የታወጀበት ዕለት ነው፤ በዚህ ዕለት የሆነው የእግዚአብሔር ፍቅርና ሰላም ቃላዊ ወይም ተምኔታዊ ኣልነበረም፤ ወይም ደግሞ በርቀት በመልእክት የተላለፈ ኣልነበረም፤ከዚህ ይልቅ ሰብእናችንን በመዋሐድ፣ በተግባር ሆኖ በመገኘት፣ እንዲሁም ለመሰጠት ዝግጁ በመሆን የተገለጠና የታየ ሰላምና ፍቅር ነው፤ እግዚአብሔር የኛን ሰላምና ፍቅር በእጅጉ የሚሻው መሆኑን ለመረዳት፣ የኛን ሰብአዊ ክዋኔ በምልአት ተዋሕዶ በመካከላችን ከመገኘት የተሻለ ሌላ ማረጋገጫ ሊኖር ኣይችልም፤ እኛ ሰዎች ለእግዚአብሔር ጠላቶቹ ተብለን በቅዱስ መጽሐፍ የተገለጽን ነን:: እግዚአብሔር ጠላቶቹን የራሱ አካል አደረጋቸው ሲባል ከመስማት የበለጠ አስደናቂ ነገር በዚህ ዓለም ምን ሊኖር ይችላል? የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት! እግዚአብሔር ሰብኣዊነታችንን በምልአት ተዋሕዶ በዓለማችን እንዲገለጥ የሆነበት ዋና ምክንያት እሱ እንዳስረዳን እኛ በሕይወት እንድንኖር ነው፤ ይህንንም ያደረገው ከሁሉ በላይ የሆነ ሌላ ገፊ ኃይል ገፋፍቶት ሳይሆን ድንበር የለሽና ፍጹም ፍቅሩ አነሣሥቶት እንደሆነ ከቅዱሳት መጻሕፍት እንረዳለን፤ የእግዚአብሔር ፍቅር እኛ ከምናውቀው ፍቅር ሁሉ በላይ መሆኑንም በዚህ እናስተውላለን፤ ለጠላቶቹ ሕይወት ፍቅርና ሰላም ሲል እነሱን ከመሆን አልፎ እስከ ቤዛዊ መሥዋዕት የሚዘልቅ ፍቅር እጅግ በጣም ታላቅ ነው፤ የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት ! እግዚአብሔር ለእኛ ያለው ፈቃድ እኛ በሕይወት በሰላምና በፍቅር እንድንኖርለት ከሆነ የእኛ ግብረ መልስም ከዚህ የተለየ ሊሆን ኣይገባም፤ እግዚአብሔር ጠላቶቹን ለማዳን እንጂ ለማጥፋት አልመጣም፤ የእኛም ሕይወት የሚጠበቀው ኣንዱ ሌላውን በማዳን እንጂ በማጥፋት እንዳልሆነ ጌታችን በቃልም በተግባርም በኣጽንዖት ነግሮናል፤ በዚህ አስተሳሰብና እምነት እንድንኖርም አዞናል፡፡ታድያ በቃሉ ለመኖርና ለእሱ ለመታዘዝ ቃል የገባን እኛ ክርስቲያኖች ይህን ሁሉ እርግፍ ኣድርገን በመተው እርስ በእርስ ለመጠፋፋት መሽቀዳደም ምን ይሉታል? ይህስ ለማን ይበጃል?የአንድ ሀገር ሕዝቦች ይመካከራሉ፣ ይቻቻላሉ፣ ይታገሣሉ፣ ጊዜ ሰጥተው ያስቡና መፍትሔ ያበጃሉ እንጂ ማን በማን ላይ ይነሣል? ይህ ለማንኛችንም አይበጀንምና ወደ ኣእምሮኣችን እንመለስ የሚል ጥሪ የወቅቱ የቤተ ክርስቲያናችን መልእክት ነው፤ በመጨረሻም፤ ይህንን የተቀደሰ በዓል ስለ ሃገራችን ዘላቂ ሰላም በመጸለይና በማሰብ እንዲሁም በልዩ ልዩ  ምክንያት የምግብ፣ የልብስና የመጠለያ እጥረት ያጋጠማቸው ወገኖቻችንን በመደገፍና በመርዳት ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ለሀገር ኣንድነትና ለሕዝብ ፍጹም ሰላም መስፈን ከልብ በመነሣሣት በዓሉን እንድናከብር አባታዊ ጥሪያችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን!! መልካም በዓለ ልደት ያድርግልን!!እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር  አሜን!አባ ማትያስ ቀዳማዊፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ታኅሣሥ ፳፱ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ምአዲስ አበባ ኢትዮጵያ ©EOTC TV

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ልደቱ ለእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ  ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመት ምሕረት Read More »

በሀገረ ስብከቱ ያሉ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የሚያስችል የምክክር መድረክ ተካሄደ!

ኤክቱስ ታኅሣሥ 27/2018 ዓ.ም በጌዴኦ ኮሬና ቡርጅ ሀገረ ስብከት የሚታዩ ዘርፈ ብዙ የአገልግሎትና የአስተዳደር ተግዳሮቶችን በዘላቂነት ለመፍታት የሚያስችል የሀሳብና የገንዘብ ድጋፍ የማሰባሰቢያ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ ሸራተን ሆቴል ተካሂዷል። መርሃግብሩ በብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል መሪነት በተቋቋመው መማክርት ጉባኤ አባላት የተዘጋጀ ነው። በዚሁ የምክክር መድረክ ላይ ብፁዕነታቸውን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የደቡብ ኦሞና የአሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው የተለያዩ ተጽዕኖ ፈጣሪ አካላት ተገኝተዋል። ​ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱን የቀድሞና ወቅታዊ ሁኔታ የሚዳስስ ሰፊ የሁኔታዎች መግለጫ (Presentation) አቅርበዋል። በመግለጫውም በሀገረ ስብከቱ ሥር በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሚታዩ ዋና ዋና ችግሮች የተዳሰሱ ሲሆን፣ በተለይም በገጠር አካባቢዎች የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት በከፊልና ሙሉ ለሙሉ ተዘግተው መቆየታቸው ትልቅ ትኩረት የሚሻ ጉዳይ መሆኑ ተመላክቷል። እነዚህን የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት በአፋጣኝ አገልግሎት እንዲጀምሩ ማድረግ በቀጣይ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር መሆኑም ገልጸዋል።​ከአብነት ትምህርት መስፋፋት ጋር ተያይዞ በሀገረ ስብከቱ ያለውን ክፍተት ለመሙላት በአሁኑ ወቅት በአንዲዳ የአዳሪ የአብነት ትምህርት ቤት መጀመሩን ገልጸዋል። ሆኖም ግን ይህ ጅምር ካለው ስፋት አንጻር በቂ ባለመሆኑ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶችን በስፋት ማደራጀትና በቋንቋ የሚያገለግሉ ካህናትና ዲያቆናትን ማፍራት እንደሚገባ በሰፊው አንስተዋል። ​በስብከተ ወንጌል ረገድም በአብዛኞቹ አድባራት ሰባክያነ ወንጌል ባለመኖራቸው ምክንያት ምዕመናን ተገቢውን መንፈሳዊ ትምህርት በማግኘት ላይ እንዳልሆኑ ተጠቅሷል። ይህን የስብከተ ወንጌል እጥረት ለመቅረፍና ወንጌልን ለሁሉም ተደራሽ ለማድረግ በአከባቢው ቋንቋ የሚያገለግሉ ሰባክያንን በማሰልጠንና በመመደብ ረገድ ሰፊ ሥራ እየተሠራ መሆኑና ይህ በቂ አለመሆኑን በመድረኩ ላይ አንስተዋል። ​የሀገረ ስብከቱን የአስተዳደር ስራዎች ከዘመኑ ጋር ለማስማማትና የአሰራር ድክመቶችን ለማስተካከል ታሳቢ ያደረጉ የለውጥ ሀሳቦችም አቅርበዋል። የሀገረ ስብከቱ መዋቅር ይበልጥ እንዲጠናከርና ለምዕመናን የሚሰጠው አገልግሎት እንዲሳለጥ አስተዳደራዊ ማሻሻያዎችን ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ለውይይቱ ተሳታፊዎች አስገንዝበዋል። ​በመጨረሻም የመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች በቀረቡት ዝርዝር ችግሮችና የመፍትሄ አቅጣጫዎች ላይ ከተወያዩ በኋላ ሀገረ ስብከቱን በሁሉም ረገድ ለመደገፍ ቃል ገብተዋል። ይህም ድጋፍ በእውቀት፣ በገንዘብና በጉልበት እንደሚሆን በመግለጽ ሀገረ ስብከቱ የተደቀኑበትን ችግሮች ተሻግሮ ተልዕኮውን እንዲወጣ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ ቃል ገብተዋል።

በሀገረ ስብከቱ ያሉ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የሚያስችል የምክክር መድረክ ተካሄደ! Read More »

Scroll to Top