<<ምልእዎንኬ ለእላ መሣብክት ማየ -ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው >> ዮሐ 2:7
➠ በወርኃ ጥር ከሚከበሩ ዐበይት በዓላት መካከል ጥር 12 ቀን የሚከበረው የገሊላ ክፍል በሆነችው በቃና ሰርግ ላይ ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገው ታላቅ ተአምር አንዱ ነው ።<<ነገርን ከስሩ ውኃን ከጥሩ >> እንዲሉ አበው ነገሩም እንዳህ ነበር ። አካል ከህልውና ተገልጾለት የሥላሴን አንድነት ሦስትነት በስፋትና በጥልቀት የተናገረው ነባቤ መለኮት በመባል የሚታወቀው ባለ ራእዩ ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ <<በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሰርግ ነበረ >> በማለት ሙሉ ታሪኩን ይጽፋል ።➠ ይህም ሰርግ የተደረገው የካቲት 23 /30 ዓ ም ሲሆን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ( የጥምቀትን በዓል የውኃው ወደ ጠጅነት መለወጥ በዓል ) ጋር እንዲከብር አባቶቻችን ስለ ወሰኑልን የጥምቀት ማግስት ጥር 12 በቃና ዘገሊላ ኢየሱስ ክርስቶስ በእመቤታችን አማላጅነት ያደረገው ታላቅ ተአምር በደማቅ ሁኔታ ይከበራል ። አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዕዳ ደብዳቤያችንን ይደመስስልን ዘንድ ( ቆላ 2:4) ጥር 11 ቀን ዕለተ እሑድ በእደ ዮሐንስ በማየ ዮርዳኖስ ተጠምቆ ( ማቴ 3:17) ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ የባሕርይ ልጅነቱን አስመስክሮ ሳይውል ሳያድር ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ ( ማቴ 4:1) ። በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከጾመ በኋላ በሦስቱ አርእስተ ኃጣውእ የመጣውን ሰይጣን ድል ነስቶ የካቲት 20 ቀን በዕለተ ቀዳም ከገዳመ ቆሮንቶስ ወጥቶ ቅዳሜ ለእሑድ ገሊላ ገብቶ አድሯል ። የገሊላ ክፍል በሆነችው በቃና የተደረገውም ሰርግ ጌታ ከገዳም ከወጣ በሦስተኛው ቀን ማለትም ማክሰኞ ነበር ። የዚህ ሰርግ ባለቤት ዶኪማስ ሲሆን በሰርጉ ላይ ይታደሙ ዘንድ ከወንድ እስከ ሴት ከመምህር እስከ ደቀ መዝሙር ያልጠራው አካል ከቶ አልነበረም ። ➠ የሚደንቅ ሰርግ ! ታዋቂ ስዎች ከላይ ምስኪኖች ከታች ፤ መምህሩ ከቤት ውጥ ደቀ መዛሙርቱ ከቤት ውጭ ያልታደሙበት ፤ሁሉም አብረው ያከበሩት ሰርግ ነበር ። በአምላካችን የተባረከ ፣ እመቤታችንና ሐዋርያት የተገኙበት ሰርግ ! የሙሽራው የዶኪማስ ልብ እንዴ በደስታ ይመላ ይሆን ? ትዳሩስ እንዴት ያምር ? ምንኛ መመረጥ ምንኛስ መታደል ነው ! የጋብቻን ቅዱስነትና ክቡርነት የተማርነውም በሰርግ ቤት ተገኝቶ ሰርግን ከባረከው የቤተ ክርስቲያን ሙሽራዋ ከሆነላት ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ነው ።ብዙዎች ግን ጋብቻን የሚረዱበትና የሚኖሩበት ሕይወት የተስተካከለ ባለመሆኑ መሰላቸትና መናቆር የበዛበት ይሆናል ። በየፍርድ ቤቱ ሳይቀር በስፋት ያለውም ጉዳይ የፍች ጉዳይ ነው ።➠ ### ጋብቻ በባልና ሚስት ፈቃድ ብቻ የሚመሠረት አይደለም ፤ በእግዘብሔር ፈቃድ ጭምር እንጂ ። ጋብቻ ስንፈልግ የምንገባበት ሳንፈልግ ደግሞ የምንወጣበትም አይደለሞ ፤ እስከ መጨረሻ የምንኖርበት እንጂ ። ጋብቻ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጸም ፣ ሁለቱም አካላት አንድ የሚሆኑበት ምሥጢርም ነው ( ሜቴ 19:6) ። ጋብቻ የተበረከ ስለሆነ የተበረኩ ልጆችም የሚገኙበት ነው (ዕብ 13:4) ። የሚገርመው ሰዎች ራሳቸው ያልፈለጉትን ግን በልጆቻቸው እንዲፈጸሙ የሚፈልጓቸው ሁለት ነገሮች አሉ ።1, የሰርጋቸው ቀን ከቤተ ክርስቲያን ጋር ሳይተዋወቁ የክርስትና ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመጡ ሰዎች ሲሆኑ2, ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውጭ በሆነ ጋብቻ የተጋቡ ሰዎች ልጆቻቸው ሥርዓት ባለመያዛቸው የሚያዝኑ ሰዎች ናቸው ። ### ልጆች ሥርዓትን ከማን ይማሩ ? ማንንስ ይከተሉ ? ተጠያቂውስ ማን ነው ?አሁን በአለንበት ዘመን በዓለም ላይ ሥርዓት አልባነት ከተስፋፋባቸው መንገዶች መካከል የጋብቻ ሥርዓት መረሳቱና ክቡር በሆነው ጋብቻ የሚወለዱ ልጆች አለመኖራቸው አንዱ ይመስለኛል ። ➠ የእመቤታችን አማለጅነት የሰርጉም ታዳሚዎች ወደ መጡበት ሳይመለሱ ለሰርጉ ይበቃል ተብሎ የታሰበው የወይን ጠጅ ድንገት አለቀ፣ አገልጋዮች የሚያደርጉት አጥተው በጭንቀት ተውጠው ሰማይ ምድሩን ማየት ጀመሩ ፣የአገልጋዮች ፊት ጠቆረ ፣ አንገታቸውንም ደፉ ፤ ማጣት ክፉ ነውና ያውም በሰርግ ቀን ሰው በተሰበሰበበት !ነገር ግን ይህን ጭንቀታቸውን ያየችው እመቤታችን ማንም ሳይነግራት << የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም >> ስትል ነበር ወደ ልጇ የማማለድ ስራዋን ያቀረበችው ። አምላካችንም የእመቤታችንን ምልጃ ከሰማ በኋላ << አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም >> አላት ፤ ማለትም አንቺ ያልሽኝን ላለማድረግ ምን ጠብ አለኝ አደርግልሻለሁ ማለት ነው ። ይህም ሊታወቅ << የሚላችሁን አድርጉ >> ነበር ያለችው ፤ ምልጃዋን እንደ ተቀበላት ታውቅ ነበርና ። የእናት ልመና ፊት አያስመልስ አንገት አያስቀልስ ነውና ነገሩ ።➠ ስለ ምልጃዋ ስለ ርኅራኄዋ <<ፈጣን ደመና >> ( ኢሳ 19:1) ብሎ ነቢዩ ኢሳይያስ የገለጣት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዛሬም ቢሆን በአማላጅነቷ ትረዳናለች ታግዘናለች ። እኛም << ወበእንተዝ ንስአል ኀቤሃ ኵሎ ጊዜ ከመ ታስተሥሪ በእንቲኣነ ኀበ ፍቁር ወለዳ ሔርት ይእቲ በኀበ ኵሎሙ ቅዱሳን – ስለዚህ ሁልጊዜ ወደ እርሷ እንለምን ከተወደደ ልጇ ዘንድ ስለእኛ ይቅር ታስብለን (ታማልደን) ዘንድ በቅዱሳን ዘንድ ቸር ናት >> እያልን እንደ ቅዱስ ኤፍሬም እንማጸናታለን ።➠ ሌላው አሳብ << ጊዜዬ ገና ነው >> የሚለው ነው ። ይህም ማለት ብዙ ትርጓሜ ቢኖረውም ዋናው አሳብ ግን ምሳሌው ወይን የሆነለት ክቡር ደሙን የዓለምን ኃጢአት ለማስተስረይ በመስቀል የሚያፈስበት ጊዜው ዕለተ ዐርብ ገና ነው ማለቱ ነበር ። ይህውም አልቀረ ጊዜው ዕለተ ዐርብ ሲደር የዓለም ኃጢአት የሚሰረይበትን ክቡር ደሙን እንኩ ጠጡ ብሎ ሰጠን (ማቴ 26:28) ። በዚህ ክቡር ደም የዓለም ኃጢአት ተወገደ (ዮሐ 1:29) ፣ አነጻን ቀደሰን << በውኂዘ ደሙ ቅዱስ አንጽሖሙ ለመሀይምናን ወለሕዝብ ንጹሓን >> እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም የዶኪማስን ሰርግ የፋሲካ ፤ የወይን ጠጁንም የክቡር ደሙ ምሳሌ አደረገው ።ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ብሉ ጠጡ የሚል ለጋስ ያለ እርሱ ማን አለ ?➠ ይህን ድንቅና ረቂቅ የሆነ ቃል በመናገር ዕለተ ሞቱን ከአስተማረ በኋላ የአገልጋዮቹን ጉድለት ይመላ ዘንድ በሰርግ ቤት የተገኘው አምላካችን << ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው>> ብሎ አዘዘ ። የእመቤታችንን ምልጃ መቀበሉን የምንረዳውም ጋኖች በውኃ እንዲመሉ በማዘዙና ውኃውን ወደ ጠጅነት በመለወጡ ነው፤ እመቤታችንም የሚላችሁን አድርጉ ነበርና ያለችው ።ባዶ የነበሩት ስድስቱም የድንጋይ ጋኖች በውኃ ከተሞሉ በኋላ በአምላካዊ ሥራው በእመቤታችን አማላጅነት ውኃውን ወደ ወይን ጠጅነት ለወጠው ፤ እግዚአብሔር ሲል ሁሉ ይለወጣልና ። ➠ የሰው ልጅ ጉድለት የሚሞላው በምን ይሆን ?የእኛስ ሕይወት የሚለወጠው መቼ ነው ? ከላይ ነጭ ነጠላ ለብሰን እንመላለሳለን ውስጣችን ግን በብዙ ነገሮች ጠቁሯል ፣ ሰብከን ስንጨርስ ቃለ ሕይወት ያሰማልን እንባላለን ሕይወት ግን ከሁላችንም ጠፍቷል ፣ ዘምረን ስንጨርስ ከጣዕሙ ብዛት የተነሣ አጥንትን የሚያለመልም የመላእክትን ዝማሬ ያሰማልን እንላለን ነገር ግን የለመለመና ጣዕም ያለው ሕይወት የለንም ። ➠ በአምላካዊ ትእዛዝ የተለወጠው የወይን ጠጅ ቀድሞ ከነበረው እጅጉን ጣፈጭ መሆኑን የቀመሰው አሳዳሪውም ሙሽራውን ጠርቶ << ሰው ሁሉ አስቀድሞ መልካሙን የወይን ጠጅ ያቀርባል ከሰከሩም በኋላ መናኛውን ፤ አንተስ መልካሙን የወይን ጠጅ እስከ አሁን አቆይተሃል >> በማለት በእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ የተለወጠውን ወይን ማድነቅ ጀመረ ። በእርግጥ እግዚአብሔር ያደረገው ነገር በሙሉ ከሁሉ በላይ ነውና መርምረንና ተናግረን ስለማንጨርሰው << ናርምም እስመ ኢንክል ፈጽሞ ጥንቁቀ ነጊረ በእንተ ዕበዩ >> እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም ሁሉን ቻይ መሆኑን አድንቀን ዝም እንላለን ። ➠ ይህም ሰርግ የሰርግ ሥርዓት ብቻ የተፈጸመበት አልነበረም ውኃውን ከውኃነት ወደ ወይን ጠጅነት በመለወጡ ምሥጢረ ሥጋዌን በሥራ ገልጦ ያሳየበት ዕለትም ጭምር እንጂ ፤ በኋላም በኬልቄዶን ጉባኤ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ የልዮናውያንን አስተምህሮ ማለትም ሁለት ባሕርይ የሚለውን ትምህርት ሲቃወም መልስ የሰጠበት ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነበር ።<< ወደ ሰርግ ቤት የተጠራ ውኃውን ጠጅ ያደረገ ማን ነው ?>> ብሎ ጠየቀ ። ሥጋ ካላችሁ የሥጋ ወደ ሠርግ ቤት መጠራት አያስደንቅም ፤ ብቻውንም ሥጋ ውኃውን ጠጅ ማድረግ አይችልም ፣ መለኮት ካላችሁ ውኃውን ጠጅ መድረግ ቢችልም ወደ ሰርግ ቤት መጠራት ግን አይችልም ብሎ እረቶበታል

