በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት የሀገረ ስብከት አቀፍ ፪ኛ ዓመት ጠቅላላ ጉባኤ በደብረ ሰላም ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን በማካሄድ ላይ ይገኛል። በመርሃግብሩ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ መልአከ ሕይወት ብርሃኑ ክፍሌ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ መልአከ ብርሃን አጥናፉ ማሞ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ፣ የሀገረ ስብከቱ የየሥራ ክፍል ኃላፊዎችና ሠራተኞች፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆች እና ጸሐፊዎች፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ጸሐፊዎች፣ ምክትል ሊቀመንበር፣ ሒሳብ ሹም፣ የማኅበረ ቅዱሳን ተወካዮች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት ተወካዮች፣ የመንበረ ጵጵስና የልማት ኮሚቴዎች እና የምዕመናን ተወካዮች ተገኝተዋል። መርሃግብሩን ብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ ጸሎተ ወንጌል፣ ኪዳን በማድረስ በጸሎት የከፈቱ ሲሆን ቀጥለውም የመርሃ ግብሩን መጀመር በይፋ አብስረዋል። በመርሃግብሩ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሕይወት ብርሃኑ ክፍሌ የአንድ ዓመት የሥራ ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን በሪፖርታቸው በሀገረ ስብከቱ በአገልጋይ እጥረት ምክንያት የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት በማይሰጥባቸው አብያተ ክርስቲያናት ከምእመናን በተሰበሰበ 1,116,000 ገንዘብና እርዳታ ለአንድ ዓመት ለ፮ ካህናት ደሞዛቸውን ችሎ አብያተ ክርስቲያናቱ የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ እንዲሁም በስድስቱ ወረዳ ቤተ ክህነት በቋንቋ ተዘዋውረው የሚሰብኩ ለአንድ ዓመት 21 ደቀመዛሙርት ለ2018 ዓ/ም በጀት ዓመት እንዲሰማሩ ምልመላ ተደርጎ የስምሪት ስልጠና ወስደው ወደ አገልግሎት መግባታቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም ሥልጣነ ክህነትን በተመለከተ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ለ90 ደቀመዛሙርት የዲቁና 16 በአጠቃላይ 106 ሥልጣነ ክህነት መሰጠቱን እንዲሁም በርካታ ኢ-አማንያን በጥምቀት የሥላሴን ልጅነት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። በመርሃግብሩ የወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆች የየወረዳ ቤተ ክህነቱን ዓመታዊ የ፩ ዓመት ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን በሪፖርታቸው በሁሉም ወረዳ ቤተ ክህነት 3372 ኢ-አማንያን መጠመቃቸውን ገልጸዋል። የመንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት በበጀት ዓመቱ 822 ኢ-አማንያን መጠመቃቸውን ገልጸው የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን በተመለከተ፣ መልካም አስተዳደርን፣ ሁለገብ ልማትን፣ የአብነት ትምህርት ቤት እና ዘመናዊ ትምህርት ቤትን፣ ሰንበት ትምህርት ቤትን በተመለከተ (የአንድነት ሰንበት ትምህርት ቤት)፣ የአደባባይ ክብረ በዓላት አከባበርን፣ የቤተ ክርስቲያን ምረቃ፣ የመሰረት ድንጋይ መቀመጥ፣ የጠበል አገልግሎት፣ የማረምያ ቤት፣ የፋይናንስ አያያዝ አስተዳደር፣ ፐርሰንት ክፍያ በተመለከተ እንዲሁም የተሀድሶን ሴራ ስለማጋለጥ የተሰሩ ሥራዎችን ገልጸዋል። የይርጋጨፌ ወረዳ ቤተ ክህነት 823 ኢ-አማንያን ማስጠመቃቸውን ገልጸው የብፁዕ አቡነ ገሪማ ጳጳስ ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ ከአድባራት አስረዳዳሪዎች ጋር የተደረጉ ውይይቶችን፣ ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት የተሰሩ ሥራዎችን፣ በአድባራቱ የተሰሩ ልማቶችን እንደአብነት የግብርና የልማት ሥራዎችን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አዲሱን ሥርዓተ ትምህርት እንዲከተሉ ለማድረግ የተሰሩ ሥራዎችን በሰፊው ገልጸዋል። በኮቾሬና ገደብ ወረዳዎች ቤተ ክህነት 273 ኢ-አማንያን መጠመቃቸውን ገልጸው በዕቅድ ዙርያ የተደረገ ውይይት፣ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናትን ለማስከፈት የተሰሩ ሥራዎችን፣ የክህነት አሰጣጥን በተመለከተ፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ለማቋቋም የተሰሩ ሥራዎችን፣ የስብከት ኬላ ማቋቋምን፣ የአቅም ማጎልመቻ ሥልጠናዎችን በተመለከተ፣ የተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናትን መለየትና ማቋቋምን በተመለከተ፣ የንግስ በዓላትን መምህራንን መመደብ መቆጣጠር የመሳሰሉትን ሥራዎች አቅርበዋል። የቡሌና ረጴ ወረዳ ቤተ ክህነት 127 ኢ-አማንያንን ማስጠመቃቸውን ገልጸው በስብከተ ወንጌል፣ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎችን፣ በሰንበት ትምህርት ቤት የተሰሩ ሥራዎችን፣ በፐርሰንት የተሰሩ ሥራዎችን፣ በአብነት ተማሪዎች ዙርያ የተሰሩ ሥራዎችን ገልጸዋል። የኮሬ ወረዳ ቤተ ክህነት 594 ኢ-አማንያንን ማስጠመቃቸውን ገልጸው የብፁዕ አባታችንን ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ የአገልጋይ እጥረት ያለባቸውን አብያተ ክርስቲያናትን አገልጋይ በመመደብ እንዲሁም ንዋየ ቅድሳትን ሟሟላት፣ ስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማስፋፋት የተሰሩ ሥራዎችን ገልጸዋል። የቡርጂ ወረዳ ቤተ ክህነት 733 ኢ-አማንያንን ማስጠመቃቸውን ገልጸው የብፁዕ ሊቀጳጳሱን ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ ስብከተ ወንጌልን ተደራሽ ከማድረግ አንጻር የተሰሩ ሥራዎች፣ ሥራዎችን ከማዘመን አንጻር የተሰሩ ሥራዎችን ሪፖርት አድርገዋል።