➠ በወርኃ ጥር ከሚከበሩ ዐበይት በዓላት መካከል ጥር 12 ቀን የሚከበረው የገሊላ ክፍል በሆነችው በቃና ሰርግ ላይ ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገው ታላቅ ተአምር አንዱ ነው ።
<<ነገርን ከስሩ ውኃን ከጥሩ >> እንዲሉ አበው ነገሩም እንዳህ ነበር ። አካል ከህልውና ተገልጾለት የሥላሴን አንድነት ሦስትነት በስፋትና በጥልቀት የተናገረው ነባቤ መለኮት በመባል የሚታወቀው ባለ ራእዩ ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ <<በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሰርግ ነበረ >> በማለት ሙሉ ታሪኩን ይጽፋል ።
➠ ይህም ሰርግ የተደረገው የካቲት 23 /30 ዓ ም ሲሆን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ( የጥምቀትን በዓል የውኃው ወደ ጠጅነት መለወጥ በዓል ) ጋር እንዲከብር አባቶቻችን ስለ ወሰኑልን የጥምቀት ማግስት ጥር 12 በቃና ዘገሊላ ኢየሱስ ክርስቶስ በእመቤታችን አማላጅነት ያደረገው ታላቅ ተአምር በደማቅ ሁኔታ ይከበራል ። አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዕዳ ደብዳቤያችንን ይደመስስልን ዘንድ ( ቆላ 2:4) ጥር 11 ቀን ዕለተ እሑድ በእደ ዮሐንስ በማየ ዮርዳኖስ ተጠምቆ ( ማቴ 3:17) ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ የባሕርይ ልጅነቱን አስመስክሮ ሳይውል ሳያድር ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ ( ማቴ 4:1) ። በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከጾመ በኋላ በሦስቱ አርእስተ ኃጣውእ የመጣውን ሰይጣን ድል ነስቶ የካቲት 20 ቀን በዕለተ ቀዳም ከገዳመ ቆሮንቶስ ወጥቶ ቅዳሜ ለእሑድ ገሊላ ገብቶ አድሯል ። የገሊላ ክፍል በሆነችው በቃና የተደረገውም ሰርግ ጌታ ከገዳም ከወጣ በሦስተኛው ቀን ማለትም ማክሰኞ ነበር ። የዚህ ሰርግ ባለቤት ዶኪማስ ሲሆን በሰርጉ ላይ ይታደሙ ዘንድ ከወንድ እስከ ሴት ከመምህር እስከ ደቀ መዝሙር ያልጠራው አካል ከቶ አልነበረም ።
➠ የሚደንቅ ሰርግ ! ታዋቂ ስዎች ከላይ ምስኪኖች ከታች ፤ መምህሩ ከቤት ውጥ ደቀ መዛሙርቱ ከቤት ውጭ ያልታደሙበት ፤ሁሉም አብረው ያከበሩት ሰርግ ነበር ። በአምላካችን የተባረከ ፣ እመቤታችንና ሐዋርያት የተገኙበት ሰርግ ! የሙሽራው የዶኪማስ ልብ እንዴ በደስታ ይመላ ይሆን ? ትዳሩስ እንዴት ያምር ? ምንኛ መመረጥ ምንኛስ መታደል ነው !
የጋብቻን ቅዱስነትና ክቡርነት የተማርነውም በሰርግ ቤት ተገኝቶ ሰርግን ከባረከው የቤተ ክርስቲያን ሙሽራዋ ከሆነላት ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ነው ።
ብዙዎች ግን ጋብቻን የሚረዱበትና የሚኖሩበት ሕይወት የተስተካከለ ባለመሆኑ መሰላቸትና መናቆር የበዛበት ይሆናል ። በየፍርድ ቤቱ ሳይቀር በስፋት ያለውም ጉዳይ የፍች ጉዳይ ነው ።
➠ ### ጋብቻ በባልና ሚስት ፈቃድ ብቻ የሚመሠረት አይደለም ፤ በእግዘብሔር ፈቃድ ጭምር እንጂ ።
ጋብቻ ስንፈልግ የምንገባበት ሳንፈልግ ደግሞ የምንወጣበትም አይደለሞ ፤ እስከ መጨረሻ የምንኖርበት እንጂ ።
ጋብቻ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጸም ፣ ሁለቱም አካላት አንድ የሚሆኑበት ምሥጢርም ነው ( ሜቴ 19:6) ።
ጋብቻ የተበረከ ስለሆነ የተበረኩ ልጆችም የሚገኙበት ነው (ዕብ 13:4) ።
የሚገርመው ሰዎች ራሳቸው ያልፈለጉትን ግን በልጆቻቸው እንዲፈጸሙ የሚፈልጓቸው ሁለት ነገሮች አሉ ።
1, የሰርጋቸው ቀን ከቤተ ክርስቲያን ጋር ሳይተዋወቁ የክርስትና ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመጡ ሰዎች ሲሆኑ
2, ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውጭ በሆነ ጋብቻ የተጋቡ ሰዎች ልጆቻቸው ሥርዓት ባለመያዛቸው የሚያዝኑ ሰዎች ናቸው ።
### ልጆች ሥርዓትን ከማን ይማሩ ? ማንንስ ይከተሉ ? ተጠያቂውስ ማን ነው ?
አሁን በአለንበት ዘመን በዓለም ላይ ሥርዓት አልባነት ከተስፋፋባቸው መንገዶች መካከል የጋብቻ ሥርዓት መረሳቱና ክቡር በሆነው ጋብቻ የሚወለዱ ልጆች አለመኖራቸው አንዱ ይመስለኛል ።
➠ የእመቤታችን አማለጅነት
የሰርጉም ታዳሚዎች ወደ መጡበት ሳይመለሱ ለሰርጉ ይበቃል ተብሎ የታሰበው የወይን ጠጅ ድንገት አለቀ፣ አገልጋዮች የሚያደርጉት አጥተው በጭንቀት ተውጠው ሰማይ ምድሩን ማየት ጀመሩ ፣የአገልጋዮች ፊት ጠቆረ ፣ አንገታቸውንም ደፉ ፤ ማጣት ክፉ ነውና ያውም በሰርግ ቀን ሰው በተሰበሰበበት !
ነገር ግን ይህን ጭንቀታቸውን ያየችው እመቤታችን ማንም ሳይነግራት << የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም >> ስትል ነበር ወደ ልጇ የማማለድ ስራዋን ያቀረበችው ። አምላካችንም የእመቤታችንን ምልጃ ከሰማ በኋላ << አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም >> አላት ፤ ማለትም አንቺ ያልሽኝን ላለማድረግ ምን ጠብ አለኝ አደርግልሻለሁ ማለት ነው ። ይህም ሊታወቅ << የሚላችሁን አድርጉ >> ነበር ያለችው ፤ ምልጃዋን እንደ ተቀበላት ታውቅ ነበርና ። የእናት ልመና ፊት አያስመልስ አንገት አያስቀልስ ነውና ነገሩ ።
➠ ስለ ምልጃዋ ስለ ርኅራኄዋ <<ፈጣን ደመና >> ( ኢሳ 19:1) ብሎ ነቢዩ ኢሳይያስ የገለጣት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዛሬም ቢሆን በአማላጅነቷ ትረዳናለች ታግዘናለች ። እኛም << ወበእንተዝ ንስአል ኀቤሃ ኵሎ ጊዜ ከመ ታስተሥሪ በእንቲኣነ ኀበ ፍቁር ወለዳ ሔርት ይእቲ በኀበ ኵሎሙ ቅዱሳን – ስለዚህ ሁልጊዜ ወደ እርሷ እንለምን ከተወደደ ልጇ ዘንድ ስለእኛ ይቅር ታስብለን (ታማልደን) ዘንድ በቅዱሳን ዘንድ ቸር ናት >> እያልን እንደ ቅዱስ ኤፍሬም እንማጸናታለን ።
➠ ሌላው አሳብ << ጊዜዬ ገና ነው >> የሚለው ነው ። ይህም ማለት ብዙ ትርጓሜ ቢኖረውም ዋናው አሳብ ግን ምሳሌው ወይን የሆነለት ክቡር ደሙን የዓለምን ኃጢአት ለማስተስረይ በመስቀል የሚያፈስበት ጊዜው ዕለተ ዐርብ ገና ነው ማለቱ ነበር ። ይህውም አልቀረ ጊዜው ዕለተ ዐርብ ሲደር የዓለም ኃጢአት የሚሰረይበትን ክቡር ደሙን እንኩ ጠጡ ብሎ ሰጠን (ማቴ 26:28) ። በዚህ ክቡር ደም የዓለም ኃጢአት ተወገደ (ዮሐ 1:29) ፣ አነጻን ቀደሰን << በውኂዘ ደሙ ቅዱስ አንጽሖሙ ለመሀይምናን ወለሕዝብ ንጹሓን >> እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም የዶኪማስን ሰርግ የፋሲካ ፤ የወይን ጠጁንም የክቡር ደሙ ምሳሌ አደረገው ።
ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ብሉ ጠጡ የሚል ለጋስ ያለ እርሱ ማን አለ ?
➠ ይህን ድንቅና ረቂቅ የሆነ ቃል በመናገር ዕለተ ሞቱን ከአስተማረ በኋላ የአገልጋዮቹን ጉድለት ይመላ ዘንድ በሰርግ ቤት የተገኘው አምላካችን << ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው>> ብሎ አዘዘ ። የእመቤታችንን ምልጃ መቀበሉን የምንረዳውም ጋኖች በውኃ እንዲመሉ በማዘዙና ውኃውን ወደ ጠጅነት በመለወጡ ነው፤ እመቤታችንም የሚላችሁን አድርጉ ነበርና ያለችው ።
ባዶ የነበሩት ስድስቱም የድንጋይ ጋኖች በውኃ ከተሞሉ በኋላ በአምላካዊ ሥራው በእመቤታችን አማላጅነት ውኃውን ወደ ወይን ጠጅነት ለወጠው ፤ እግዚአብሔር ሲል ሁሉ ይለወጣልና ።
➠ የሰው ልጅ ጉድለት የሚሞላው በምን ይሆን ?
የእኛስ ሕይወት የሚለወጠው መቼ ነው ?
ከላይ ነጭ ነጠላ ለብሰን እንመላለሳለን ውስጣችን ግን በብዙ ነገሮች ጠቁሯል ፣ ሰብከን ስንጨርስ ቃለ ሕይወት ያሰማልን እንባላለን ሕይወት ግን ከሁላችንም ጠፍቷል ፣ ዘምረን ስንጨርስ ከጣዕሙ ብዛት የተነሣ አጥንትን የሚያለመልም የመላእክትን ዝማሬ ያሰማልን እንላለን ነገር ግን የለመለመና ጣዕም ያለው ሕይወት የለንም ።
➠ በአምላካዊ ትእዛዝ የተለወጠው የወይን ጠጅ ቀድሞ ከነበረው እጅጉን ጣፈጭ መሆኑን የቀመሰው አሳዳሪውም ሙሽራውን ጠርቶ << ሰው ሁሉ አስቀድሞ መልካሙን የወይን ጠጅ ያቀርባል ከሰከሩም በኋላ መናኛውን ፤ አንተስ መልካሙን የወይን ጠጅ እስከ አሁን አቆይተሃል >> በማለት በእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ የተለወጠውን ወይን ማድነቅ ጀመረ ። በእርግጥ እግዚአብሔር ያደረገው ነገር በሙሉ ከሁሉ በላይ ነውና መርምረንና ተናግረን ስለማንጨርሰው << ናርምም እስመ ኢንክል ፈጽሞ ጥንቁቀ ነጊረ በእንተ ዕበዩ >> እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም ሁሉን ቻይ መሆኑን አድንቀን ዝም እንላለን ።
➠ ይህም ሰርግ የሰርግ ሥርዓት ብቻ የተፈጸመበት አልነበረም ውኃውን ከውኃነት ወደ ወይን ጠጅነት በመለወጡ ምሥጢረ ሥጋዌን በሥራ ገልጦ ያሳየበት ዕለትም ጭምር እንጂ ፤ በኋላም በኬልቄዶን ጉባኤ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ የልዮናውያንን አስተምህሮ ማለትም ሁለት ባሕርይ የሚለውን ትምህርት ሲቃወም መልስ የሰጠበት ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነበር ።
<< ወደ ሰርግ ቤት የተጠራ ውኃውን ጠጅ ያደረገ ማን ነው ?>> ብሎ ጠየቀ ። ሥጋ ካላችሁ የሥጋ ወደ ሠርግ ቤት መጠራት አያስደንቅም ፤ ብቻውንም ሥጋ ውኃውን ጠጅ ማድረግ አይችልም ፣ መለኮት ካላችሁ ውኃውን ጠጅ መድረግ ቢችልም ወደ ሰርግ ቤት መጠራት ግን አይችልም ብሎ እረቶበታል ። ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ነው ። አምላክ ፍጹም ሰው እንደ መሆኑ ወደ ሰርግ ቤት ተጠርቷል ፤ ሰውም ፍጹም እምላክ እንደ መሆኑ ውኃውን ወደ ወይን ጠጅ ቀይሮታል ። ከተዋሕዶ በኋላ ይህ የሥጋ ፣ ይህ የመለኮት የምንለው ሥራ የለም ። በፍጹም ተዋሕዶ ከሁለት አካል አንድ አካል ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ ስለሆነ ሥራውን ሠራ ይባላል እንጂ ።
ይህም ተአምር በገዳመ ቆሮንቶስ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲራብ አይቶ ሰይጣን ርሑቅ ብእሲ መስሎት ነበርና የባሕርይ አምላክ መሆኑን ያሳየበት የመጀመሪያውና ታላቁ ተአምር ነው ።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር !!!
