ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል በጎላ ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን በሚገኘው የጸበል ሥፍራ ላይ በመገኘት ጸሎተ ወንጌል፣ ኪዳን አድርሰው የጸበል ሥፍራውን ባርከዋል።
በመርሃግብሩ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ መልአከ ብርሃን ቀሲስ አጥናፉ ማሞ ፣ የመንበረ ጵጵስናና ወናጎ ወረዳ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጠበብት መሪጌታ መሰረት፣ የወረዳ ቤተ ክህነቱ ዋና ጸሐፊ ሊቀ ኅሩያን ቀሲስ እሸቱ ዋለ፣ ቀሲስ ሄኖክ የቤተ ክርስቲያኑ የሰበካ ጉባኤ ሊቀ መንበር፣ የደብሩ ካህናትና ዲያቆናት፣ የደብሩ የሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያንና ምዕመናን ተገኝተዋል።
ብፁዕነታቸው በመርሃግብሩ ትምህርት የሰጡ ሲሆን በትምህርታቸው የእግዚአብሔር መልአክ በሚያናውጸው ውሃ ብዙዎች ከደዌ ሥጋ ይፈወሱ እንደነበር፣ ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው ምራቁን በአፈር እንትፍ ብሎ ተአምራትን እንዳደረገ አንስተው ዛሬም በዘመናችን እግዚአብሔር የሰጠንን ይህንን ጸበል አክብረን ብንይዘው እና በእምነት ብንጠቀመው ብዙ ተአምራትን እንደሚያደርግ በሰፊው ገልጸው መርሃግብሩን በጸሎት ፈጽመዋል።



