ኤክቱስ የካቲት 24/2018 ዓ.ም
ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ ኮሬና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ለጀመረው “አንድ ብር ለሰብዓዊነት” የገቢ ማሰባሰቢያ ዘመቻ የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል። ብፁዕነታቸው ለዘመቻው ስኬት 10,000 (አስር ሺህ) ብር የለገሱ ሲሆን፣ በተጨማሪም 2,000 (ሁለት ሺህ) ብር በመክፈል የማኅበሩ የዕድሜ ልክ አባል ሆነዋል።
ይህ የገንዘብ ድጋፍ የተበረከተው የጌዴኦ ዞን ቀይ መስቀል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ለአንድ ወር የሚቆይ የሀብት ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ይፋ ባደረገበት ወቅት ነው። ብፁዕነታቸው በወቅቱ ባስተላለፉት መልእክት እንዲህ ያሉ ሰብአዊ ተግባራት በችግር ውስጥ ለሚገኙ ወገኖች ያላቸውን ፋይዳ በማብራራት ማኅበሩ እያከናወነ ያለውን ተግባር እንደሚያደንቁ ገልጸዋል።
በተጨማሪም ብፁዕነታቸው በመላው በጌዴኦ ዞን የሚገኙ ሁሉም በዚህ የበጎ አድራጎት ጥሪ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ አባታዊ ጥሪ አቅርበዋል። ድጋፉ የተቸገሩ ወገኖችን ሕይወት ለመታደግና ሰብአዊ ቀውሶችን ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውም ብፁዕነታቸው አስገንዝበዋል።

Pingback: finasteride hair loss